Thursday, July 14, 2016

በጎንደር የተቀሰቀሰው ህዝባዊ ተቃውሞ ወደ ሌሎች አካባቢዎች እየተዛመተ ነው

ኢሳት (ሃምሌ 7 ፥ 2008)

ከቀናት በፊት በጎንደር ከተማ የተቀሰቀሰዉ ህዝባዊ ተቃዉሞ ሐሙስ ወደ ደባርቅ ከተማና ዙሪያዋ ባሉ አካባቢዎች በመዛመት ላይ መሆኑን ነዋሪዎች ለኢሳት ገለጡ ።
ሰሞኑን በመንግስት የፀጥታ ሀይሎች የተገደሉ ሰዎችን ሐሙስ የቀብር ስነ-ስርአት ቢካሄድም ስነ-ስርአቱ ወደ ተቃዉሞ መቀየሩንና ነዋሪዎች ህዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ (ህወሐት)ን የሚያወግዙ  መፈክሮችን ሲያሰሙ መዋላቸዉ ታዉቋል።
በከተማዋ የተሰማራ የፀጥታ ሀይሎች ተቃዉሞዉን ለመበተን አስለቃሽ ጢስን መጠቀም ቢጀምሩም ተቃውሞዉ በቁጥጥር ስር ሊውል አለመቻሉን ለደህንነታቸዉ ሲሉ ስማቸዉን መግለፅ ያለፈለጉ ነዋሪዎች ከዜና ክፍላችን ጋር ባደረጉት ቃለ-ምልስ አስረድተዋል።

እለቱ የቀብር ስነ-ስርአት ብቻ አልነበረም ሲሉ የገለፁት ነዋሪዎች የአማራና የቅማንት ማህበረሰብ አንድ መሆኑን ያሳየበት እለት ነዉ ሲሉ አንድ የጎንደር ከተማ አዛውንት ገልፀዋል።
ሀሙስ ወደ ደባርቅ ከተማ የተዛመተዉ ይኸዉ ህዝባዊ ተቃዉሞ ለበርካታ ሰዎች እስራትና የአካል ጉዳት መድረስ ምክንያት መሆኑን ከነዋሪዎቹ ለመረዳት ተችሏል።
በሽሬ ከተማ ሁለት ተሽከርካሪዎች መቃጠላቸዉን የተናገሩት ነዎሪዎች በሽሬ ከተማና ዙሪያዋ ተመሳሳይ ተቃዉሞ እየተካሄደ መሆኑን አክለዉ አስታዉቀዋል።
በተለያዩ ከተሞችና ወረዳዋች እየተካሄደ ባለዉ ህዝባዊ ተቃውሞ ነዋሪዎች የታሰሩ ሰዎች እንዲፈቱ ጥያቄን እያቀረቡ እንደሆነም ታውቋል።
ከቀናት በፊት ከትግራይ ክልል መጥተዋል የተባሉ የደህንነት አባላት የወልቃይት ጠገዴ ኮሚቴ አባላትን በመያዝ ያደረጉትን ሙከራ ተከትሎ በጎንደር ከተማ ተቃዉሞ መቀስቀሱን የሚታወስ ነዉ።
የወልቃይት ወረዳ በህገ-ወጥ መንገድ መካለሉን በመግለፅ ላይ የሚገኙ ነዋሪዎች ወረዳዉ በአማራ ክልል ስር መተዳደር እንዳለበትና የማንነት ጥያቄን ሲያነሱ መቆየታቸዉን ይታወቃል።
የመንግስት ባለስልጣናት የማንነት ጥያቄዉ እልባትን አግኝተዋል ቢሉም የወልቃይት ጠገዴ ተወላጆች ጥያቄያቸዉ ህጋዊ ምላሽን እንዳላገኘ በመግላፅ ላይ ናቸዉ።
የአማራ ክልልም ሆነ የፌደራል መንግስት በጎንደር ከተማና ዙሪያ እየተካሄደ ስላለዉ ግጭት ምላሽን ያልሰጡ ሲሆን የመንግስት ኮሚዩንኬሽን ጉዳዩች ሚኒስተር አቶ ጌታቸዉ ረዳ አርብ መቀመጫዉን በአዲስ አበባ ላደረጉ የዉጭ ሀገር መገናኛ ብዙሃን በሀገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ መግለጫ እንደሚሰጡ ለመረዳት ተችሏል።

No comments:

Post a Comment