Friday, July 1, 2016

በአዲስ አበባ ከተማና አካባቢው ዜጎችን ከቤት ንብረታቸው የማፈናቀል ድርጊት በአስቸኳይ እንዲቆም ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ሰመጉ) ጠየቀ

ኢሳት (ሰኔ 24 ፥ 2008)

በአዲስ አበባ ከተማና አካባቢው ዜጎችን ከቤት ንብረታቸው የማፈናቀል ድርጊት በአስቸኳይ እንዲቆም ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ሰመጉ) ጠየቀ።
ዜጎች ለረጅም ዓመታት በይዞታነት ግብር ሲከፍሉበት ከቆዩበት ቦታ “ህገወጥ ናችሁ” ብሎ ማፈናቀል በምንም መልኩ ተቀባይነት ያለው ድርጊት አለመሆኑን ድርጅቱ ባወጣው አስቸኳይ ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቋል።
በቦሌ ክ/ከተማ ወረገኑ የሚባል አካባቢን ጨምሮ በተለያዩ ክፍለከተሞችና በአዲስ አበባ ከተማ ዳርቻ ለረጅም ጊዜ ከኖሩበት ቦታ በአፍራሽ ግብረሃይል ቤቶችን ማፍረስ አግባብ አለመሆኑን ሰመጉ በሪፖርቱ ላይ ጠቅሷል። በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክ/ከተማ ቀርሳና ኮንቶማ 19ሺ 246 ነዋሪዎች በቤት ማፍረሱ ሂደት እንደተፈናቀሉ ተገልጿል። በተመሳሳይ መልኩ፣ በተክለሃይማኖት ከ250 በላይ አባዎራዎች ለብዙ አመታት ከኖሩበት ቦታ ለቃችሁ ውጡ መባላቸውን ለሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ መናገራቸው በሰመጉ ሪፖርት ላይ ሰፍሯል። በኢርቱ ተክለሃይማኖት እንዲሁ 169 የቤተሰብ ሃላፊዎች ለአመታት ከኖሩበት ቦታ በመፈናቀላቸው በከፍተኛ ችግር ላይ መሆናቸው ተነግሯል።

ለችግሩ ህጋዊ አማራጭ መፈለግ ሲገባ የማፍረሱ ሂደት ትዕግስት የጎደለውና ሃይል የተቀላቀለበት በመሆኑ ለበርካታ ሰዎች ሞት፣ መቁሰል፣ መታሰርና መፈናቀል መንስዔ መሆኑን የሰመጉ ሪፖርት ያስረዳል።
መንግስት ከማስተር ፕላን ጋር አይጣጣምም በሚል ቤቶቻቻው እየፈረሱ ያሉባቸው ዜጎች ለሰመጉ በአካል ቀርበውና በተወካዮቻቸው አማካኝነት ሪፖርት እንዳቀረቡ ለማወቅ ተችሏል።
እርምጃው እየተወሰደ ያለው ክረምት እየገባ ባለበት ወቅት በመሆኑ እየፈረሱ ባሉት ቤቶች ውስጥ ሲኖሩ የነበሩ አስር ሺዎች የሚቆጠሩ ሴቶች፣ ህጻናትና አረጋውያን ከፍተኛ ችግር ላይ ተዳርገው እንደሚገኙ ገልጿል።
ማንኛውም ዜጋ በሃገሪቱ አካባቢዎች የመዘዋወር፣ ቤት ንብረት የማፍራት መብት እንዳለው ቢደነገግም፣ መንግስት ደግሞ በተቃራኒው የዜጎችን መብት በመግፈፍ ቤቶቻቸውን ያፈርስባቸዋል፣ ያባራቸዋል ሲል ሰመጉ ክስ አቅርቧል።
አሁን በመንግስት እየተፈጸመ ያለው ድርጊት የሰብዓዊ መብት ድንጋጌዎችን የሚቃረን በመሆኑ፣ ወደ አላስፈላጊ ግጭት ከመገባቱ በፊት መንግስት የዜጎችን መብት የማክበር ግዴታ እንዳለበት አሳስቧል።
በመሆኑም ለህይወት መጥፋት፣ ለአካል መጉደል፣ ንብረት መውደም ተጠያቂ የሆኑ አካላትን ለፍርድ እንዲቀርቡ፣ ለችግሩ ሰላማዊ መፍትሄ እንዲሰጠው፣ ቤት ለፈረሰባቸው ካሳ እንዲከፈላቸው ሰመጉ በመግለጫው አሳስቧል።

No comments:

Post a Comment