Friday, July 8, 2016

ትምህርት ሚኒስቴር የሁለተኛ ደረጃ መልቀቂ ፈተና መውጣቱን በተመለከተ መግለጫ ለመስጠት ፈቃደኛ ባለመሆኑ ተማሪዎች ተረጋግተው ለመፈተን አልቻሉም



ሐም ( አንድ ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በመጪው ሳምንት መጀመሪያ ላይ የሚሰጠው የሁለተኛ ደረጃ መልቀቂያ ፈተና ከፈተናው ቀን በፊት ለኢሳት መላኩን የተመለከተ ዘገባ ከቀረበ በሁዋላ፣ ኢሳት የትምህርት ሚኒስቴር ባለስልጣናት አስተያየት እንዲሰጡበት ለማድረግ ላለፉት 2 ቀናት ተደጋጋሚ ጥረት ሲያደርግ ቢቆይም፣ በሚኒስቴሩ በኩል መረጃ የሚሰጠው አካል ለማግኘት ባለመቻሉ ትክክለኛነቱ ላይ አስተያየት ለመስጠት ሳይችል ቀርቷል።

“ፈተናው ተሰርቆ ወጥቷልና እባካችሁ አጣሩልን” በማለት የጠየቁን ወገኖች፣  26 ገጽ ያለው የእንግሊዝኛ የፈተና ወረቀት በማመሳከሪያነት ከላኩልን በሁዋላ፣ የኢሳት የኢዲቶሪያል ቦርድ መረጃው በኢንተርኔት እንዳይለቀቅ ወስኖ ነበር። ትምህርት ሚኒስቴር የዜናውን ይፋ መሆን ተከትሎ መልስ ባይሰጠም፣ ለኢሳት የደረሰው የፈተና ቅጅ ወረቀት ከትናንት ጀምሮ በኢንተርኔት በስፋት መሰራጨቱን የኢዲቶሪያል ቦርዱ አረጋግጧል።

ተማሪዎች ፈተናቸውን ተረጋግተው እንዲወስዱ ትምህርት ሚኒስቴር ሃላፊነት ተሰምቶት መግለጫ መስጠት እንዳለበት የኢሳት የኢዲቶሪያል ቦርድ በድጋሜ ጠይቋል። የሁለተኛ ደረጃ መልቀቂያ ፈተናን ለመስጠት የድርጅት አባላት የሆኑ መምህራን በብዛት ተመርጠው በዳግማዊ ሚኒሊክ ትምህርት ቤት ስልጠና ሲሰጣቸው ቆይቷል።

No comments:

Post a Comment