Monday, July 18, 2016

በሶማሊያ የኢትዮጵያ ወታደሮች 13 ንጹሃን ዜጎችን ገደሉ

በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአፍሪካ ሰላም አስከባሪነት ጦር አሚሶም ስር ሶማሊያ ውስጥ የተሰማራው የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ምንም ዓይነት የጦር መሳሪያ ያልታጠቁ 13 ሰላማዊ የሶማሊያ ዜጎች ላይ የጅምላ ግድያ መፈጸሙ ተዘግቧል።

ከባይደዋ ከተማ በስተምእራብ 30 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው አውዲኒያ አቅራቢያ የግፍ ግድያው መፈጸሙን የአካባቢው ነዋሪዎች ገልጸው፣ ከሞቱት13 ዜጎች በተጨማሪ ቁጥራቸው በውል የማይታወቅ ዜጎች ላይ ከፍተኛና ቀላል ጉዳት ደርሶባቸዋል።

የኢትዮጵያ ወታደሮች በተለይ የቁርአን የሃይማኖት መምህራን ላይ ከቤታቸው እያወጡ ለይተው በተናጠል ጥይት አዝንብበዋቸዋል ሲሉ በስፍራው የነበሩ የአውዲኒያ ከተማ ነዋሪ እማኝነታቸውን ሰጥተዋል።
ወይዘሮ ሳዲዮ አሊ ሃሰን የተባሉ በጥቃቱ አባታቸውን በሞት ያጡ ነዋሪ ፣ ”ደካማው ሕመምተኛው ሽማግሌው አባቴ እቤት ውስጥ ሆኖ ቁርአን በመቅራት ላይ እያለ ነበር ወታደሮቹ እቤት ውስጥ ገብተው በጭካኔ አባቴን የገደሉብኝ” ሲሉ ሁኔታውን በምሬት ተናግረዋል።
”አወዲን ገብተው የኢትዮጵያ ወታደሮች በጭካኔ ሰላማዊ ዜጎቻችንን ሲገሉ በስፍራው አንድም የአልሸባብ ሰራዊት የሌለ ሲሆን ምንም ዓይነት ውጊያም አልተካሄደም። የእኔ አባት በግፍ ከተገደሉት አንዱ ነው” ሲሉ አክለው ተናግረዋል።
በተደጋጋሚ በማእከላዊና ደቡባዊ የሶማሊያ ግዛቶች በኢትዮጵያ የሰላም አስከባሪ ጦር ተደጋጋሚ ግድያዎች ይፈጸማሉ።
የትናንቱን የጅምላ የግፍ ግድያ አስመልክቶ የአፍሪካ የሰላም አስከባሪ ጦር አሚሶም መግለጫ አለመስጠቱን ማእረግ ሚዲያ ዘግቧል።

No comments:

Post a Comment