Wednesday, December 10, 2014

ህዝብን በማይሽር ቁስል አየጎዱ በፕሮፓጋንዳ ማከም አይቻልም:

Minilik Salsawi (ምንሊክ ሳልሳዊ).
ወቅሰን ወቅሰን ወንጅለን ወንጅለን የሰለቸን ለመስማትም የታከተን ነገር ቢኖር ያለፉት ስርአቶች ላይ እና ሌላው ላይ ማሳበብን አንዱን ከአንዱ ለማፋጀት ማፈራረጅን መጠቋቆምን የመሳሰሉት ኢሕአዴጋዊ ባህርያት ናቸው::ወያኔ ኢሕኣዴግ የጭንቅ ነገር ውስጥ ሲገባ አጣብቂኙ መላወሻ ሲያሳጣው ያቆሰለውን የረገጠውን ህዝብ በማደናበሪያ ፕሮፓጋንዳ መሸንገል እና ማከም መልሶም መዋጥ አንደኛው አምባገነን ባህርይው ነው::ከዚህ በፊት እንደገለጽኩት ታሪክ ይቅር የማይለው ከባድ መንግስታዊ ወንጀል በሙስሊም ወገኖቻችን ላይ ተፈጽሟል::http://minilik-salsawi.blogspot.com/2014/…/blog-post_23.html በኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴዎች ላይ የደረሰው ግርፍት እና መከራ ቁስሉ የኔም ነው።


በኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ላይ ሽብር ግድያ እስር ድብደባ እንግልት በጅምላ አፈሳ ዘረፋ ንጥቂያ እና ከፍተኛ የሆነ ኢሰብአዊነት እና ጭፍጨፋ በመንግስት ነኝ ባይ ሃይሎች በይፋ በአደባባይ ተፈጽሟል::ይህንን መንግስታዊ ሽብር የማይሽር ጠባሳ በመላው ኢትዮጵያውያን ላይ ጥቁር ነጥብ አስቀምጧል::ይህንን ጠባሳ በሃሰት ፕሮፓጋንዳ እና በሽንገላ አሊያም በማደናበሪያ ቃላት ማከም አይቻልም::የመንግስታዊውን ሽብርተኝነት ችግር በሌላ እምነት ላይ እንደ ሰበብ በማላከክ አሊያም የተቃዋሚ ፖለቲከኞችን አጀንዳ በመለጠጥ በፍረጃ ሌላውን ከመወንጀል ይልቅ የኢትዮጵያውያን ሙስሊሞችን ጥያቄዎች እና የኮሚቴውን መፈታት ጥያቄ በአስቸኳይ መመለስ ሊዘነጋ የማይገባ ጉዳይ ሲሆን የሃይማኖት ነጻነትን ማረጋገጥ እና በሃይማኖቶች ላይ የሚፈጸም መንግስታዊ ውንብድናን ማስቆም የእያዳንዱ ዜጋ ሃገራዊ ግዴታ መሆኑንም ማውቅ ያስፈልጋል::

ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ለሃገራቸው እና ለነጻነታቸው ከጥንት ጀምሮ ምን ያህል ቀናኢ እና መስዋትነት የከፈሉ በመክፈልም ላይ ያሉ እንቁ ዜጎች መሆናቸውን መንግስታዊው አሸባሪም ይሁን አዋቅጭ አማሳኝ ነን የሚሉ ሁሉ ሳይወዱ በግዳቸው ሊውጡት የሚገባ ታሪካዊ እና ታላቅ እወነት ነው::የወያኔው መንግስት የሙስሊሙን የሃይማኖት ነጻነት ጥያቄ ላለመመለስ አንዴ በሙስሊም መንግስት ምስረታ ሲወነጂል አልሆን ሲለው በተቃዋሚ ፓርቲዎች አጀንዳነት ሲቆላልፍ እምቢ ሲለው በሌሎች ሃይማኖት የውስጥ መርመስመስ ሽብራዊ አደጋ ሲፈርጀው እምቢ ሲለው የችግሩ መንስኤ ጥቂቶች ናቸው አሊያ የኦርቶዶክሶች እጅ በሚሉ የተለያዩ ማሳበቢያዎች ቢፈጥርም ይህ ንቃተ ህሊናው ከአሸባሪው መንግስት በልጦ በ እጥፍ ያደገው ሕዝብ ራስህ መንግስት አሸባሪ ነህ ሙስሊም ህዝቦቼን እያሸበርክ ነው እያለ እየነገረው ያለበት ሁኔታ በስፋት በመላው አገሪቱ አይተናል እያየንም ነው::

እውነትን ለመዋጥ ሁል ግዜ የሚከብደው አሸባሪው የወያኔ ስርአት አሁንም ማጭበርበሪያ መንገዶችን በመጠቀም በፖለቲከኞች መካከል የሚፈጥረውን መከፋፈል አይነት ስራዎች ለመስራት ቆርጦ የተነሳው ወያኔ ህዝብ ከሱ ቀድሞ መንቃቱን እንኳን መረዳት አለመቻሉ ጭፍንነቱን ያሳያል::አይኑን ገልጦ ሩቅ ለመመልከት ያዳገተው ወያኔ በተለያየ መልኩ የሙስሊም ወገኖችን ጥያቄ ለመፈረጅ ያማሰነው ስትራቴጅ ስላልተሳካለት እንዲሁም የምርጫው መድረስ አጣብቂኝ ውስጥ ስለከተተው በፕሮፓጋንዳ እና የራሱን መንግስታዊ ሃጢያት በሌላው ላይ ለመለጠፍ እየዳዳው ይገኛል::በሙስሊም ወገኖቻችን ላይ የደረሰው ሰቆቃ የማእከላዊ ቶርች እና ስቃይ እያንዳንዳችን እንዳንተኛ እና ነገ በኛ በማሰብ ለኮሚቴዎቹ ፍትህ በንቃት እንድንሰራ ብርታት ሰቶናል።

ስለዚህ አንድ አምባገነን ስርአት ታግለን ለመጣል የግዴታ እያንዳንዱ ዜጋ እስር ቤት ገብቶ መታሰርን እና መገረፍን መመልከት ሳይሆን ወንድሞቻችን በ እስር ቤት ያሳለፉት መከራ እንደመከራችን አይተን ሲነጋ ደሞ ወደ እኛ ቤት እንደሚመጣ አስበን ለታሰሩት ሃቀኛ ፍትህን ለኛም የማይሸራርፍ መብቶቻችንን ለማግኘት መታገል ግዴታችን መሆኑን ማወቅ ያስፈልገናል።ለዘመናት ተሳስሮ እና ተከባብሮ የኖረን ህዝብ ለማፋጀት ዘመን በወለዳቸው የአይሁዶች ቋንቋ አሸባሪ አክራሪ እየተባሉ ዜጎች የሚደርስባቸው መከራ እንዲቆም እያንዳንዳችን መስእዋት መሆን አለብን። የአብሮነታችን ተምሳሌት ለአለም ያስተማረውን የአያቶቻችንን የአንድነት ፍቅር ደግመን በዚህ ትውልድም ማሳየት አለብን ። አምባገነኖች ጠንክረን ከታገልናቸው ቀዳዳው ሁሉ ስለሚጠብባቸው ተፍረክርከው ይጠፋሉ። መላው ኢትዮጵያውያን ለዚህ አሸባሪ እና አጭበርባሪ አደናጋሪ መንግስታዊ አክራሪ ሳንዘናጋ በጋራ ተያይዘን በአንድ ሃገራዊ አጀንዳ አምባገነኖችን በመቅበር በ እጃችን ያለውን ነጻነት በማረጋገጥ ለነገው ትውልድ አዲሲቷን
 የጋራ ኢትዮጵያን በማስረከብ ታላቅ የሆነውን የዜግነት ድርሻችንን እና ሃላፊነታችንን እንድንወጣ ለማሳሰብ እወዳለሁ:: Minilik Salsawi

No comments:

Post a Comment