Wednesday, September 5, 2018

የአየር ትራፊክ ተቆጣጣሪዎች ለተጨማሪ የምርመራ ጊዜ በእስር ላይ እንዲቆዩ ተደረገ

(ኢሳት ዲሲ–ነሐሴ 30/2010) አድማ በማስተባበር ተጠርጥረው የታሰሩት ዘጠኝ የአየር ትራፊክ ተቆጣጣሪዎች ለተጨማሪ የምርመራ ጊዜ በእስር ላይ እንዲቆዩ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ አሳለፈ።

በሌላም በኩል በአድማ ላይ የቆዩት የአየር ትራፊክ ተቆጣጣሪዎች ዛሬ ስራ መጀመራቸውን መንግስታዊ መገናኛ ብዙሃን በዘገባቸው አስፍረዋል።


የ10 እጥፍ የደሞዝ ጭማሪ በመጠየቅ ከነሐሴ 21/2010 ጀምሮ አድማ ላይ የቆዩት የአየር ትራፊክ ተቆጣጣሪዎች ዛሬ ሙሉ በሙሉ እንዴት እንደተመለሱ በዝርዝር የተገለጸ ነገር ባይኖርም በደሞዝ ጭማሪው ዙሪያ ጥናት እየተደረገ መሆኑን የኢትዮጵያ ሲቪል አቬሽን ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኮለኔል ወሰንየለህ ሁነኛው ለመገናኛ ብዙሃን ገልጸዋል።

አድማውን አስተባብረዋል በሚል ሰኞ ዕለት በቁጥጥር የዋሉት ዘጠኙ የአየር ትራፊክ ተቆጣጣሪዎች ፊርማዎችን አስመስሎ በመፈረም ጭምር ሕገወጥ ድርጊት እንደፈጸሙ ፖሊስ ገልጿል።

ተጠርጣሪዎቹ ያቀረበነው ጥያቄ የመብት ጥያቄ በመሆኑ ዋስትና ልንከለከል አይገባም ቢሉም ፍርድ ቤቱ ተጨማሪ 8 የምርመራ ቀናትን ለፖሊስ በመፍቀድ ወደ ወህኒ ቤት እንዲመለሱ አድርጓል።

ረዥም አመታት ማስቆጠሩ የተገለጸው የኢትዮጵያ ሲቪል አቬስን ሰራተኞች የመብት ጥያቄ በሚያዚያ ወር 2010 ላይ ወደ ርምጃ አምርቷል።

በኢትዮጵያ ሲቪል አቬሽን እንቅስቃሴ ላይ ጉልህ ተጽእኖ ማድረሱና የአለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃንም ርዕስ መሆኑ ይታወሳል።

በዚህ ወቅት በስራ ላይ የነበሩ ሁለት የአየር ትራፊክ ሰራተኞች አድማ በመምታታቸው በኢትዮጵያ ቦሌ አለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ የነበሩት በረራዎች ላይ ከ30 እስከ 40 ደቂቃ መስተጓጎል መድረሱ ይታወሳል።

ከነሐሴ 21 ጀምሮ የተመታውን አድማ ተከትሎ የኢትዮጵያ ሲቪል አቬሽን ጡረተኛ የነበሩ ትራፊክ ተቆጣጣሪዎችንና የውጭ ሰዎችን በማሳተፍ መስተጓጎሉን ለመግታት መንቀሳቀሳቸው ታውቋል።

የኬንያ የአየር ትራፊክ ሰራተኞች ማህበር ከአዲሶቹ የአየር ትራፊክ ሰራተኞች ጋር በትክክል መናበብ አልተቻለም በማለት ቅሬታውን አቅርቧል።

የኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለስልጣናት የኬንያውያኑን ርምጃ ለአድማው የሚደረግ ትብብር ሲሉ ወቀሳውን ውድቅ አድርገዋል።

 አድማ ማድረግ መብት አይደለም እንዴ?ለምን የአድማው መሪዎች ይታሰራሉ?የሚለው ጥያቄ በስፋት በመነሳት ላይ ነው። የመንግስት ሃላፊዎች ደግሞ በእንዲህ ያለ የስራ መስክ መሰል ርምጃ መውሰድ መብት አይደለም ወንጀል ነው ሲሉ በመከራከር ላይ ናቸው

No comments:

Post a Comment