Monday, September 24, 2018

በጋምቤላ 5 ሰዎች በጸጥታ ሃይሎች ተገደሉ

(ኢሳት ዲሲ–መስከረም 14/2011) በጋምቤላ ከተማ 5 ሰዎች በጸጥታ ሃይሎች ተገደሉ።
ባለፉት ሁለት ቀናት በከተማው ህዝብ የተነሳውን ተቃውሞ ተከትሎ ፖሊስ በወሰደው የሃይል እርምጃ ከ20 በላይ ሰዎች መቁሰላቸውንም የደረሰን መረጃ ያመለክታል።
በሀገሪቱ ለውጥ ቢኖርም በጋምቤላ ግን ለውጡን ለማየት አልቻልንም በሚል የተጀመረው ተቃውሞ ተጨማሪ የሰው ህይወት ሊያጠፋ እንደሚችል ነዋሪዎች ስጋታቸውን በመግለጽ ላይ ናቸው።
በጋምቤላ ከተማ የሚገኙ ወጣቶች በክልሉ አስተዳደራዊ ለውጥ እንዲመጣ እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ ናቸው።
በተለይም የክልሉ ፕሬዝዳንት ጋት ሉዋክ ቱት የሕዝብ ችግሮችን አልፈቱም በሚል ከስልጣን እንዲነሱ በመጠየቅ የተቃውሞ ሰልፍ ለማድረግ ሲሞክሩ በክልሉ የጸጥታ ሃይሎች ተገድለዋል።

በዚህ ውስዝግብ የተነሳ የመከላከያና የፌደራል ፖሊስ አባላት ጣልቃ ገብተው 4 ሰዎች ሲገደሉ ይህንኑ በመቃወም ሰልፉ በመባባሱ ተጨማሪ አንድ ሰው መገደሉ ታውቋል።
በዶክተር አብይ የሚመራውን የለውጥ ሃይል ወጣቶቹ እንደሚደግፉ ቢገልጹም በጋምቤላ ግን ተመሳሳይ ለውጥ አልመጣም በሚል ተቃውሞ እያሰሙ ይገኛሉ።
በጋምቤላ በሶስት አቅጣጫዎች የተለያዩ ማህበረሰቦች በሚኖሩበት የጋምቤላ ክልል ውጥረት መንገሱ ይነገራል።
የጋምቤላ ክልል አስተዳደር በከተማዋ የተፈጠረውን ግጭት በተመለከተ እስካሁን የሰጠው መግለጫ የለም።
በጋምቤላ ያለው ሁኔታ ግን እስካሁን አልተረጋጋም።በጋምቤላ የተፈጸመውን ግድያ በተመለከተ ለአዲሲቱ ኢትዮጵያ የጋራ አጋርነት ድርጅት ዋና ስራ አስፈጻሚና የሰብአዊ መብት ተከራካሪው አቶ ኦባንግ ሜቶ የውግዘት መግለጫ መስጠታቸው ታውቋል።
አቶ ኦባንግ ሜቶ እንዳሉት መብት ለመጠየቅ በወጡ ሰልፈኞች ላይ ግድያ መፈጸሙ በምንም መንገድ ቢሆን ተቀባይነት የለውም።

No comments:

Post a Comment