Monday, September 3, 2018

የአማራ ሕዝብ ክፉዎች በፈጸሙበት በደልና ግፍ ሳቢያ ከኢትዮጵያዊ ማንነቱ ዝቅ አይልም ሢል አርቲስትና አክቲቪስት ታማኝ በየነ ተናገረ።

 ( ኢሳት ዜና ነሐሴ 28 ቀን 2010 ዓ/ም ) አክቲቪስት ታማኝ ይህን ያለው፣ ዛሬ በባህር ዳር ስታዲዬም አቀባበል ላደረገለት እጅግ በርካታ የባህር ዳርና አካባቢው ሕዝብ ባደረገው ንግግር ነው። የባህ ዳር ስታዲየም አርቲስት ታማኝን ለመቀበል ከየ አቅጣጫው እየተግተለተለ በመጣው የሰው ጎርፍና በፈጣን ፈረሰኞች ከአፍ እስከ ገደፉ መሙላት የጀመረው፣ ገና ከማለዳው አንስቶ ነው። ለረዥም ሰዓታት በትዕግስት ሢጠባበቅ የቆዬው በስታዲየሙ የታደመው ሕዝብ ፣አክቲቪስት ታማኝ በስፍራው ሢደርስ
ኢትዮጵያዊነትን ከፍ ባደረገ መልኩ በልዩ የደስታ እና የእልልታ ስሜት ደማቅ አቀባበል አድርጎለታል። ለታማኝ የእንኳን ደህና መጣህ ንግግር በማድረግ ፕሮግራሙን የከፈቱት፣ ባህር ዳር አውሮፕላን ማረፊያ ሢደርስ አቀባበል ያደረጉለት የብአዴን ማዕከላዊ ኮሚቴ አባሉ አቶ ብናልፍ አንዷለም ናቸው። በማስከተል ንግግር ያደረገው አክቲቪስት ሙሉ አቀን ተስፋው፣ ከወቅቱ ሀገራዊ ፖለቲካ አኳያ የአማራን -በአማራነት የመደራጀት አስፈላጊነት በሰፊው አብራርቷል። “የአማራ መደራጀት ለኢትዮጵያ ብስራት እንጂ መርገም አይሆንም” ሲልም ተናግሯል ሙሉቀን። “በመጨረሻም ሶስት ነገር እነግራችኋለሁ” ያለው አክቲቪስት ሙሉቀን “ አንደኛ እንደራጅ፣ ሁለተኛ እንደራጅ፣ ሶስተኛ እንደራጅ”በማለት መልዕክቱን ቋጭቷል። ተከታዪ ተናጋሪ የእለቱ የክብር እንግዳ አክቲቪስት ታማኝ በየነ ባህር ዳርን እሱ ከሀገር ሲወጣ ከነበረችበት ሁኔታ በተለዬ መልኩ ተለውጣና አድጋ እንዳገኛትና የአማራ ክልል ዋና ከተማ እንደሆነች በማውሳት “ይሁንና አማራ ክልል የለውም! የአማራ ክልሉ ኢትዮጵያ ነች!!!” በማለት ነው መልዕክቱን ማስተላለፍ የጀመረው። ታማኝ፦ በቅርቡ ወደ ብሔር አደረጃጀት እየገቡ ላሉ የአማራ ተወላጆች ባስተላለፈው መልዕክትም “የደረሰባችሁ በደል፣በደሌ ነው!! የደረሰባችሁ ስቃይ-ስቃዬ ነው!! ኢትዮጵያዊነታችሁን እንድትለቁ የሚያቃጥል ጸረ -አማራ ድርጊት ተፈጽሞባችኋል። ያን ሁሉ ያደረጉት ኢትዮጵያዊነታችሁን ሊያስለቅቋችሁ ነው !! ይሁንና ዛሬም፣ ነገም፣ ከነገ ወዲያም ኢትዮጵያዊ ነን!!”ብሏል። «ጣልያን አማራን የገደለ 25 ብር ይሰጥ ነበር። ያ ግዜ ተመልሶ መጥቶ አማራ በገደል ሲወረወር አይተናል።» ያለው አርቲስት ታማኝ “ሆኖም ከትግራይ የወጡ ጥቂት ክፉዎች በፈጸሙት በደል፣ ፍጹም ኢትዮጵያዊው የሆነውን የትግራይን ሕዝብ በጥላቻ ማዬት ተገቢ አይደለም” በማለት ከሁሉም ብሄርተሰቦች ጋር በፍቅርና በመዋደድ እንዲኖሩ ጥሪ አቅርቧል። ትልቁ የትግራይ ሕዝብ በጥቂት ክፉ ሹመኞች እንደማይወከል በአጽንዖት የተናገረው አርቲስት ታማኝ፤ “ ይልቁንም የትግራይን ህዝቡ ከናንተም ከኛም መጥፎዎች ይበቅላሉ። በነዚህ ክፉዎች ምክንያት የአንድነት ገመዳችን አይበጠስም እንበላቸው”ብሏል። “ትናንት በትግሉ ጊዜ “የኦሮሞ ደም የኔም ደም ነው! በማለት ተንኮለኞች ሊያፈርሱት የተነሱት የኢትዮጵያዊነት ገመድ ፈጽሞ እንደማይበጠስ በተግባር ያሳዬው የአማራ ሕዝብ፤ አሁንም በበደልና በግፍ በመማረር አያቶቹ በአጥንትና በደማቸው አስከብረው ካወረሱት ኢትዮጵያዊነት ዝቅ አይልም ሲልም አክቲቪስት ታማኝ ተናግሯል። አክሎም፦”ኢትዮጵያ የጋራ ቤታችን ናት! ኢትዮጵያ እናታችን ናት!!በኢትዮጵያ ያሉት ሁሉም ዜጋዎች ወንድሞቻችንና እህቶቻችን ናቸው”ብሏል። በየንግግሮቹ መሀከል “ይደገም! “በሚል የህዝብ ድምጽ ታጅቦ ስለኢትዮጵያውያን አንድነት ጥልቅ መልዕክት ያስተላለፈው አርቲስት ታማኝ ፤ያለፉትን በደሎችና ቂም በቀሎች በመተው ስለወደፊቷ ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ ግንባታ በጋራ መሥራት እንደሚያስፈልግ አሣስቧል። እሱ በራሱ ከሀገር ሲወጣ መገፋት እንደደረሰበት ባወሳበት በከትናንት በስቲያ የአዲስ አበባ ንግግሩ “ ከሀገሬ ተገፍቼ ብወጣም፣ ቂም ይዜ አልተመለስኩም” ማለቱ ይታወሳል።

No comments:

Post a Comment