Thursday, September 6, 2018

በሰኔ 16ቱ የቦንብ ጥቃት ተጠርጣሪ በሆኑት አቶ ተስፋዬ ኡርጌ ላይ ተጨማሪ የጊዜ ቀጠሮ ተሰጠባቸው

 ( ኢሳት ዜና ጳግሜን 01 ቀን 2010 ዓ/ም ) በአዲስ አበባ ከተማ መስቀል ዓደባባይ ሰኔ 16 ቀን 2010 ዓ.ም በተጠራው የምስጋና እና የመደመር የድጋፍ ሰልፍ ወቅት በተፈጸመው የቦንብ ጥቃት እጃቸው አለበት ተብለው ከተጠረጠሩት አንዱ የሆኑት አቶ ተስፋዬ ኡርጌ ላይ መርማሪ ፖሊስ ያቀረበውን ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ፍርድ ቤቱ ተቀበለ። ፖሊስ ለፌደራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት 1ኛ የወንጀል ችሎት ባቀረበው አቤቱታ በተጠርጣሪው አቶ
ተስፋዬ ኡርጌ ላይ በርካታ የምርመራ ስራዎችን እየሰራ መሆኑን ለፍርድ ቤቱ አሳዉቋል። አስፈላጊውን ምርመራ አጠናቆ ለማቀረብ ተጨማሪ የሰው ምስከር ቃል ለመቀበልና ከብሄራዊ መረጃና ደኅንነት ቢሮ የተደረገ የስልክ ልውውጥ የድምፅ ቅጂ ማስረጃን ለማቅረብ የ14 ቀን ተጨማሪ የጊዜ ቀጠሮ እንዲሰጠው ጠይቋል። ተጠርጣሪው ተከሳሽ አቶ ተስፋዬ ኡርጌ በበኩላቸው በተደጋጋሚ የተንዛዛ የጊዜ ቀጠሮ መጠየቁን ለፍርድ ቤቱ በመግለጽ ዋስትና እንዲፈቀድላቸው አሊያም አጭር ቀየጊዜ ቀጠሮ እንዲሰጥላቸው ችሎቱን ጠይቀዋል። መርማሪ ፖሊስም በበኩሉ ተከሳሹ ያቀረቡትን አቤቱታ እንደማይቀበለው በመግለጽ፤ ጉዳዩ ውስብስብ ከመሆኑ አኳያ ፍርድ ቤቱ በትኩረት እንዲያው ጠይቋል። ተከሳሽ አቶ ተስፋዬ ኡርጌ በዋስትና ቢወጡ ለመረጃ ግብአት የሚሆኑ ምስክሮችን ሊያሸሹብን ይችላሉ ሲልም የዋስትና ጥያቄውን እንደሚቃወም ለችሎቱ አመልክቷል። ፍርድ ቤቱም የተከሳሹን ይግባኝ ሳይቀበለው ቀርቷል። መርማሪ ፖሊስ ይቀረኛል ያለውን ተጨማሪ ምርመራ አጠናቆ እንዲቀርብ ለመስከረም 5 ቀን 2011 ዓ.ም ተለዋጭ የጊዜ ቀጠሮ ሰጥቷል።

No comments:

Post a Comment