Tuesday, September 12, 2017

የሶማሊ ልዩ ሃይል በኦሮሞ ህዝብ ላይ የሚፈጽመውን ግድያ የሚያወገዝ ህዝባዊ ተቃውሞ እየተካሄደ ነው

(ኢሳት ዜና መስከረም 2 ቀን 2010 ዓም)
ካለፉት ሁለት ወራት ጀምሮ በአቶ አብዱ ሙሃመድ ኡመር የሚመራው የሶማሊ ልዩ ሃይል ታጣቂዎች በግዛት ማስፋፋትና በድንበር ይገባኛል ስም በመቶዎች የሚቆጠሩ የኦሮሞ ተወላጆችን መግደላቸውንና ጥቃቱም መቀጠሉን ተከትሎ፣ ድርጊቱን የሚያወግዙ ተቃውሞዎች በተለያዩ ከተሞች ሲካሄድ ውሎአል።
በአወዳይ፣ ደደር ፣ ቆቦ፣ ጭናክሰን፣ ሃሮማያ፣ ሂርና፣ ጨለንቆ፣ ጉርሱምና ሌሎችም ከተሞች ጠንካራ ተቃውሞዎች እየተካሄዱ ሲሆን፣ ህዝቡ በዝምታ እያስጠቃን ነው የሚሉትን ኦህዴድን ፣ ከሶማሊ ታጣቂዎች ጀርባ ሆኖ ጥቃቱን ያቀነባብራል ያሉትን ህወሃትንና እና የሶማሊ ክልል
መሪዎችን እያወገዙ ተቃውሞአቸውን ሲገልጹ ውለዋል። ህዝቡ ከዚህ በተጨማሪ የህዝቡ መብት እንዲከበርና የታሰሩ የፖለቲካ እስረኞች እንዲፈቱ ጠይቋል።
በአወዳይ ሌሊት ላይ በተጀመረው ተቃውሞ እስካሁን ባለው መረጃ 5 ሰዎች ሲገደሉ፣ በርካታ ዜጎችም መቁሰላቸውም ታውቋል። አንድ የወታደር ጂፕ መኪናን ጨምሮ 6 መኪኖች ሲቃጠሉ፣ ወደ አዲስ አበባ፣ ጅጅጋና አጎራባች ከተሞች የሚደረገው የትራንስፖርት አገልግሎት ተቋርጧል። ከአወዳይ ወደ ሶማሊ ክልል ይላክ የነበረው ጫት እንዲቋረጥ ተደርጓል።
ከፍተኛ ተቃውሞ በተካሄደበት ደደር ከተማ ደግሞ ወጣቶች ድምጻቸውን እያሰሙ ወደ መስተዳደር ጽ/ቤት ሲያመሩ በተከፈተባቸው ተኩስ 3 ወጣቶች በጽኑ ቆስለው ሆስፒታል ገብተዋል።
የሶማሊ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ አብዲ መሃመድ በክልሉ የሚኖሩ የኦሮሞ ተወላጆች አካባቢውን ለቀው እንዲወጡ በማዘዛቸው በመቶዎች የሚቆጠሩ የኦሮሞ ተወላጆች ሃረር ከተማ የገቡ ሲሆን፣ ተጨማሪ ተፈናቃዮች መንገድ ላይ መሆናቸውን አንድ ስማቸው እንዳይገለጥ የፈለጉ የአካባቢው ባለስልጣን ተናግረዋል። ከቀብሪደሃርና ጭናክሰን የተፈናቀሉት ቦቲጋ እየተባለ በሚጠራው ፖሊስ ጣቢያ ውስጥ የተጠለሉ ሲሆን፣ ሌሎች ደግሞ ምስራቅ ሃረርጌ ጽ/ቤት ውስጥ ይገኛሉ።
ሁኔታው እጅግ አሳሳቢ መሆኑን የሚገልጹት የአካባቢዎች ነዋሪዎች፣ ለዘመናት በአንድነት ሲኖሩ የነበሩትን የሶማሊ እና ኦሮሞ ተወላጆችን ለማጋጨት የተለያዩ የትንኮሳ እርምጃዎች እየተወሰዱ ነው። ትናንት የጉርሱም አስተዳዳሪ የተገደሉ ሲሆን፣ ገዳዮችን በተመለከተ የተለያዩ አስተያየቶች እየተሰጡ ነው። ግድያውን የሶማሊ ልዩ ሃይል አባላት እንደፈጸሙት የሚናገሩ ወገኖች ያሉ ሲሆን፣ አንዳንድ ሰዎች ግን ድርጊቱን የሁለቱን ክልል ህዝብ ለማጋጨት ሆን ተብሎ የተቀናበረ ነው ይላሉ።

No comments:

Post a Comment