Tuesday, September 19, 2017

በኢሬቻ በዓል የተገደሉ ንጹሃን ዜጎች ሞት እንዲያጣራ እና ለመጪው የኢሬቻ ክብረ በዓልም ቅድመ ጥንቃቄ እንዲደረግ ሲል ሂውማን ራይትስ ወች ጠይቋል

ዓለምአቀፉ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት ሂውማን ራይትስ ወች ባለፈው ዓመት መስከረም 22 ቀን 2009 ዓ.ም በቢሾፍቱ ከተማ አቅራቢያ ሆራ አርሰዲ ሐይቅ የኢሬቻ በዓል ክብረ በዓል በማክበር ላይ እያሉ በግፍ የተገደሉት እና የተጎዱ ንጹሃን ኢትዮጵያዊያን ዜጎች ጉዳይ በዓለምአቀፍ ማኅበረስብ ገለልተኛ አካል እንዲጣራ ጠይቋል። በዘንድሮው ዓመት ለሚደረገውም የኢሬቻ በዓል ላይ ተመሳሳይ እልቂት እንዳይፈጸም ቅድመ ጥንቃቄ እንዲደረግ ሲል አሳሰበ። ሂውማን ራይትስ ወች በሞቶዎች የሚቆጠሩ ሰላማዊ ዜጎች ያለቁበትን ዘግናኝ እልቅት ሊከሰት የቻለው የጸጥታና ደኅንነት ኃይሎች መውጫ መንገዶችን በመዝጋት አስለቃሽ ጋዝና ከመጠን በላይ ኃይል በመጠቀማቸው መሆኑን ከቪዲዮ መረጃ ጋር አያይዞ አርቅቧል።
በሰው በተጨናነቀው በዓል ላይ የኢትዮጵያ መንግስት የጸጥታ ኃያሎች ''በእሳት ላይ ነዳጅ አርከፍክፈዋል'' ሲል ለእልቂቱ መባባስ ቀዳሚው ተጠያቂዎች ታጣቂዎቹ መሆናቸውን በ33 ገጽ ሪፖርቱ አትቷል። ከኢትዮጵያ ሕዝብ አርባ ሚሊዮን
የሚሆኑት የኦሮሞ ብሔር ተወላጆች በሚያከብሩት የኢሬቻ በዓል የዝናቡን ማክተም እና የጸደይን መግባት አስመልክቶ የሚከበር የምስጋና በዓል ነው። በወቅቱ ተረጋግጠው ከሞቱት በተጨማሪ ነፍጥ ባነገቡ የጸጥታ ኃይሎች ሆን ተብሎ ተተኩሶባቸው የተገደሉ ብዙሃን ሰላማዊ ኤጎች መኖራቸውን ሪፖርቱ አመላክቷል።

በአፍሪካ የሂውማን ራይትስ ወች ተመራማሪ ፌሊክስ ሆርን ''ባለፈው ዓመት በፀጥታ ኃይሎች የተፈጸመውን ዓይነት አሰቃቂ እና ያልተመጣጠነ የኃይል እርምጃ በዘንድሮው ዓመትም ሊደገም አይገባውም!'' በማለት ቅድመ ጥንቃቄ እንዲገደረግ ጠይቀዋል።
በተጨማሪም ፊሊክስ ሆርን አክለው ''ለዘመናት የቆዩ ቅሬታዎች እና ብሶቶች አሁንም ምላሽ አላገኙም። የዘንድሮው ዓመት የኢሬቻ በዓል በውጥረትና ስጋት የበዛበት ሊሆን ይችላል። መንግስትና የጽጥታ ኃይሎች ከበዓሉ አስቀድሞ ሆኖ በበዓሉ እለት የዜጎችን ሕይወት ለመታደግ እና ውጥረቶችን ለማርገብ አስፈላጊውን ቅድመ ጥንቃቄ መውሰድ ይገባቸዋል።'' ሲሉ አሳስበዋል።
በአገር ውስጥ እና ባሕርማዶ የሚገኙ ከሃምሳ በላይ የሚሆኑ በስፍራው የነበሩ የዐይን እማኞችን፣ የሕክምና ባለሙያዎችን ኢትዮጵያዊያንን ቃለመጠይቅ በማድረግ፣ ጨምሮ በርካታ የቪዲዮ ጥናቶችን በማድረግ ሂዩማን ራይትስ ዎች ሪፖርቱን አጠናቅሯል። ከደርዘን በላይ የሚሆኑት ምስክሮች ግድያው በመንግስት ሆን ተብሎ የተቀናበረ ድርጊት መሆኑን ተናግረዋል። ሂውማን ራይት ወች በዚህ ላይ ምንም ዓይነት መረጃ እንዳላገኘ ጠቅሷል። ነገርግን ባለፉት ሁለት ዓመታት ውስጥ የተፈጸሙት ኢሰብዓዊ ጭፍጨፋዎችን ተከትሎ በሕዝቡ ዘንድ ከፍተኛ ቁጣ በመኖሩ የዘንድሮው ዓመት የኢሬቻ በዓል የእልቂት መነሻ ሊሆን እንደሚችል ሂውማን ራይትስ ወች ስጋቱን ገልጿል።
ከአዲስ አበባ ደቡባዊ ምስራቅ 40 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ከምትገኘው ባለፈው ዓመት ከተከሰተው የቢሾፍቱ ከተማ የኢሬቻ ዘግናኝ ጭፍጨፋ በኋላ በመላ አገሪቱ ከፍተኛ ውጥረት ነግሷል። የኢሬቻን እልቂት በመቃወም ድምጻቸውን ካሰሙ ሰላማዊ ዜጎች ውስጥ ከአንድ ሽህ በላይ የሚሆኑት በጸጥታ ኃይሎች በግፍ ተገለዋል። ከ10 ሽህ በላይ የሚሆኑት ደግሞ በተለያዩ ማሰቃያ እስር ቤቶች ውስጥ ታጉረው ሰቆቃ /ቶርቸር/እየተፈጸመባቸው ይገኛሉ።
ገዥው መንግስት ከዚህ በፊት ከሚደረጉ ክብረበዓላት በተለየ ባለፈው ዓመት በአየር ላይ ዝቅ ብለው የሚያንዣብቡ ሄሊኮፍተሮችን ጨምሮ ከፍተኛ የሆነ የጸጥታ እና የደህንነት ኃይሎችን አሰማርቷል። በገዥው ፓርቲ የሚደገፉ የሃይማኖት አባቶችንም በሥፍራው እንዲገኙ ተደርገዋል። ይህም ለውጥረቱ መባባስ እና ለእልቁቱ መከሰት ከፍተኛው ሚና እንዳለው ሪፖርቱ አትቷል። አንድ ወጣት መድረክ ላይ በመውጣት ፀረመንግስት መፈክር አሰምቷል።
በወቅቱ ታጣቂዎች ወዲያውኑ ሃላፊነት ሳይሰማቸው አስለቃሽ ጋዝ በመተኮስ መውጫ በሮችን በመዝጋታቸው ለብዙሃን ሰላማዊ ዜጎች ተረጋግጠው እንዲሞቱ ምክንያት ሆነዋል። በግርግሩ ወቅት የተወሰኑት በአቅራቢያው በሚገኝ ጉድጓድ ውስጥ በመግባት ሕይወታቸው አልፍዋል። የተቀሩት ደግሞ የታጣቂዎችን ተኩስ ሸሽተው በሚያመልጡበት ወቅት በሆራ ሃይቅ ውስጥ ሰምጠው ሞተዋል። በስፍራው የነበሩ አብዛሃኛው እማኞች እንዳሉት ከሟቾቹ ውስጥ አብዛሃኞቹ ሆን ተብለው
በተተኮሰ ጥይት መገደላቸውን እና መቁሰላቸውን ተናግረዋል።
ከኢሬቻው እልቂት በኋላ በመላው የኦሮሞ ብሔር ተወላጆች ዘንድ ቁጣን በመቀስቀሱ በገዥው ፓርቲ ንብረቶች ላይ ጥቃት ተፈጽሟል። ይህን ተከትሎ ገዥው ፓርቲ ለአስር ወራት የዘለቀውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ለማውጣት መገደዱን ሂውማን ራይትስ ወች በሪፖርቱ አመላክቷል።
አንድ ገመቹ የተባለ የ26 ዓመት ወጣት የኢሬቻውን ጭፍጨፋ አስመልክቶ ሲናገር ''ያለፈው ዓመት የኢሬቻ እልቂት እስከዛሬ እኛ ከምናውቃቸው ጭፍጨፋዎች ሁሉ የከፋው ነው። ይህንን ም ቁጣችንን ከዓመት በላይ በዘለቀ ሕዝባዊ ተቃውሞዎች እየገለጽን እንገኛለን። የእኛን ቅዱስ በዓል በቁጥጥራቸው ስር ለማድረግ መሞከራቸው በሕዝቡ ዘንድ ቁጣ አስከተለ። ነገርግን እስከዛው ድረስ እኛ ሰላማዊ ተቃውሞ ነበር ያደረግነው። ከዓመት በላይ ሲገሉን የነበሩት ወታደሮች በኢሬቻ ላይም በሰላማዊ ተቃዋሚዎች ላይ እንደለመዱት ጥይቶችን በማርከፍከፍና አስለቃሽ ጋዝ በመተኮስ ሰዎች ተረጋግጠው እንዲሞቱ አደረጉ። ለዛ ሁሉ ንጹሃን ሕዝብ ሞት ምክንያቱ እነሱ ናቸው።'' ሲል ምስክርነቱን ሰጥቷል።
የፎቶግራፍ እና የቪዲዮ ማስረጃዎች ቢኖሩም ከዘግናኙ የኢሬቻ እልቂት በኋላ እንኳን መንግስት ለሟቾቹ የሃዘን መግለጫ ከመስጠትና ታጣቂዎች የጦር መሳሪያ አልያዙም የሚል ምክንያት ከመደርደር ውጪ የእልቂቱን መነሾ በገለልተኛ አካል እንዲጣራ አልተደረገም። በተቃራኒው ጠቅላይ ሚንስትሩ የጸጥታ ኃይሎች የወሰዱት እርምጃ አስመልክቶ ሰላም እና ስርዓት ለማስከበር ያደረጉት ጥረት እንደሚያስመሰግናቸው መግለቻ የሰጡ ሲሆን ሌሎች የገዥው ፓርቲ ከፍተኛ ባለስልጣናት በበኩላቸው ጭፍጨፋው በጸረሰላም ኃይሎች የተፈጸመ ነው ሲሉ አሳበዋል።
በገለልተኛ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተቋማት ማጣራትና ምርመራ እንዳይደረግ እገዳ በማድረግ በገዥው ፓርቲ በሚደገፈው የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን በኩል ሪፖርት አቀርቧል። የኢትዮጵያ የሰብአዊ መብት ኮሚሽን የመንግስት ወገንተኛ ተቋም ስለሆነ ሚዛናዊነት የጎደለው ሪፖርቱ ተቀባይነት የለውም ሲል ሂውማን ራይትስ ወች ሪፖርቱን አጣጥሎታል።
ሰላማዊ ዜጎች በሚበዙበት አካባቢ መሳሪያ የታጠቁ ኃይሎች እንዳይገኙ ዓለምአቀፍ ሕጎች ስለሚያስገድዱ ይህንን የኢትዮጵያ መንግስት እዲይያከብር ሲል ሂውማን ራይትስ ወች ሪፖርቱን አጠቃሏል።

No comments:

Post a Comment