Tuesday, September 19, 2017

ወደ ኬንያ የተለከው ስኳር እየተበላሸ ነው

ኢትዮ-ኬንያ ድንበር ላይ ስኳር ጭነው ላለፉት 43 ቀናት የቆሙት 110 መኪኖች፣ የጫኑት ስኳር እየተበላሸ እንሱም ለከፍተኛ ችግር እየተዳረጉ መሆኑን ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ ሹፌሮች ገልጸዋል። 
በአገር ውስጥ ከፍተኛ የስኳር እጥረት ተፈጥሮ ባለበት በዚህ ወቅት ለውጭ ምንዛሬ ሲል 100 ሺ ኩንታል ስኳር ለኬንያ መንግስት የሸጠው አገዛዙ፣ ስኳሩ ከጥቅም ውጭ በመሆኑ የውጭ ምንዛሬውም ሳያገኝ፣ ጉዳቱ ለሹፈሮችና ለቤተሰቦቻቸው መትረፉን 110 ባለንብረቶች፣ 110 ሹፌሮችና የሹፌሮች ቤተሰቦች እና እረዳቶች በገራ በመሆን ለኢሳት በላኩት አቤቱታ አመልክተዋል።
ከነሃሴ 3 ቀን 2009 ዓም ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ያለ ስራ የቆሙት አሽከርካሪዎች ጉዳያቸውን ከማህበራቸው ጀምሮ በሚኒስቴር ደረጃ እስካሉ ባለስልጣናት ቢያቀርቡም የሚሰማቸው አላገኙም። “ በባንክ እዳና በእቁብ የተገዙት መኪኖች 

እስከዛሬ ድረስ 42 ቀናት በመቆማቸው ምክንያት፣ ንብረታቸው በእዳ ከመወሰዱም በላይ ቤተሰቦቻቸው ለረሃብና እንግልት “ ተዳርገዋል።
ስኳሩ በዝናብ እና በጸሃይ ምክንያት ቀለሙ እየተቀየረና እየቀለጠ በመሆኑ፣ 44 ሺ ኩንታል ስኳር ከጥቅም ውጭ እየሆነ መምጣቱን ሹፌሮች ገልጸዋል። ባለፈው አርብ ምሽት ላይ ማንነታቸው ያልታወቁ ሃይሎች ስኳር ጭነው በቆሙት 2 መኪኖች ላይ ጥይት በመተኮሳቸው መስታውቶቻቸው መሰበራቸውም ታውቛል።
የስኳር ኮርፖሬሽን የኮርፖሬት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክተር አቶ ጋሻው አይችሉም፥ የኬንያ መንግስት ጥያቄን መሰረት በማድረግ ኢትዮጵያ ለኬንያ 100 ሽህ ኩንታል ስኳር ባለፈው ግንቦት ወር ላይ ስምምነት ላይ መድረሷን ገልጸዋል። ስኳሩን የገዛው የኬንያው ድርጅት ብራይት ድንበር ተሻጋሪ የደረቅ ጭነት ማመላለሻ ባለንብረቶች ማህበር ጋር ስምምነት በመፈጸም፣ ስኳሩ ወደ ኬንያ እንዲገባ ለማድረግ መሞከሩንና በኬንያ ህግ አንድ መኪና መጫን የነበረበት 280 ኩንታል ሆኖ እያለ 400 ኩንታል በመቻኑ ችግሩ መፈጠሩን ባለስልጣኑ ተናግረው ነበር።
እኝሁ ባለስልጣን ችግሩ በመፈታቱ ሚኖቹ ከነሃሴ 21 ቀን ጀምሮ ወደ ኬንያ እንደሚንቀሳቀሱ ገልጸው የነበረ ቢሆንም፣ መኪኖቹ ግን አሁንም አለመንቀሳቀሳቸውን ሹፈሮች ገልጸዋል።
አቶ ጋሻው ግንቦት ላይ በተደረሰው ስምምነት መሰረት ኢትዮጵያ ለኬንያ መንግስት ማቅረበ የነበረባት 100 ሺህ ኩንታል ስኳር የነበረ ቢሆንም፣ የብራይት የደረቅ ጭነት ማመላለሻ ባለንብረቶች ማህበር በገባው ውል መሰረት በአፋጣኘ ትራንስፖርት ባለማቅረቡ 44 ሺ ኩንታል ስኳር ብቻ እንዲላክ መደረጉንና ማግኘት የነበረባቸውን የውጭ ምንዛሬ በጊዜ እንዳያገኙ ምክንያት እንደሆነ ለገዢው ፓርቲ ልሳናት ገልጸው ነበር።
በአሁኑ ጊዜ ሁሉም ፋብሪካዎች ለእደሳት ስራ በማቆማቸው ፣ በእድሳት ወቅት ለመለዋወጫ እና ለጥገና የውጭ ምንዛሬ የሚያስፈልግ በመሆኑና ይህን እጥረት ለመሙላት ስኳሩ ወደ ኬንያ መላኩን ገልጸዋል።
በኢትዮጵያ ውስጥ ከፍተኛ የስኳር እጥረት በመፈጠሩ ህዝቡ በገበያዎች ላይ በበቂ መጠን ለማግኘት ተቸግሯል። ቀበሌዎችም ስኳር በበቂ ሁኔታ ማከፋፈል አልቻሉም። የስኳር ዋጋም በኪሎ እስከ 40 ብር እየተሸጠ ነው።

No comments:

Post a Comment