Wednesday, September 13, 2017

(ኢሳት ዜና፣ መስከረም 3 ቀን 2009 ዓም) የሶማሊ ልዩ ሃይል አባላት በኦሮሞ ህዝብ ላይ እየፈጸሙ ያለውን ጥቃት የሚያወግዙ የተቃውሞ ሰልፎችና አድማዎች ተጠናክረው ቀጥለዋል።
ዛሬ በነበረው ተቃውሞ በርካታ ሰዎች በአጋዚ ወታደሮች ተገድለዋል።
በመቶዎች የሚቆጠሩ የኦሮሞ ተወላጆች በሶማሊ ልዩ ሃይል አባላት መገደላቸው ያስቆጣቸው ዜጎች ተቃውሞአቸውን በተለያዩ መንገዶች በመግለጽ ላይ ናቸው። በባቢሌ ህዝቡ ወደ አደባባይ በመውጣት ተቃውሞውን ሲያሰማ ውሎአል። ተቃውሞውን ለመበተን ፖሊሶች ወደ ሰልፈኞች ተኩሰዋል።
በሃረር ደግሞ ሱቆች እንዲሁም በከተማዋ የሚሰሩ የባጃጅ አሽከርካሪዎች ስራ በማቆም ተቃውሞአቸውን ሲገልጹ ውለዋል።
በርካታ ወታደሮች ቁጥጥር እያደረጉ በሚገኙባት ድሬዳዋ ከተማ ደግሞ በመልካ ጀብዱና በአንዳንድ ቀበሌዎች ሱቆች ተዘግተዋል። የትራንስፖርት አገልግሎትም ተቋርጧል።
በካራሚሌ በነበረው ተቃውሞ 1 ሰው ሲገደል 5 ሰዎች ደግሞ መቁሰላቸውን ወኪላችን የአካባቢውን ነዋሪዎች ዋቢ በማድረግ ገልጿል።

በአወዳይ ከትናንት ጀምሮ ሲካሄድ በዋለው ተቃውሞ ከ5 ያላነሱ ሰዎች ተገድለዋል። በርካታ የህወሃት ንብረት የሆኑ የሰላም አውቶቡሶች ወድመዋል። ዛሬ የምስራቅ እዝ ወታደሮች ወደ ከተማዋ በብዛት በመግባት ወጣቶችን ለመያዝ አሰሳ ሲያደርጉ ውለዋል።
ከጂጂጋ፣ ውጫሌ፣ ቀብሪበያህና ሌሎችም ከተሞች በሃይል የተባረሩ 500 የሚሆኑ የኦሮሞ ተወላጆች ሃረር ከተማ የደረሱ ሲሆን፣ የአካባቢው ህዝብ ምግብ እየያዘ በመሄድ ድጋፉን ገልጿል። ከ300 በላይ ተፈናቃዮች ደግሞ በገልባጭ መኪኖች ተጭነው ባቢሌ ከተማ ደከታ በሚባለው አካባቢ እንደሰፍሩ ተደርጓል።
በጅጅጋ ፖሊሶችና እና የክልሉ ባለስልጣናት ያደራጁዋቸው ሰዎች ቤት ለቤት እየዞሩ የኦሮሞ ተወላጆችን መታወቂያ በማየት ወደ ማጎሪያ ቦታ ወስደዋቸዋል። የሶማሊ ተወላጆች የኦሮሞ ወንድሞቻቸውና እህቶቻቸው ከክልሉ እንዲወጡ መደረጉን አጥብቀው እየተቃወሙት መሆኑን ጅጅጋ የሚኖሩ ወጣቶች ተናግረዋል። የኦሮሞ ወገናቸውን በመደበቅ ከመፈናቀል ለመታደግ እየሞከሩ መሆኑንም ወጣቶች ይናገራሉ። )
ዘጋቢያችን እንደገለጸው በኢትዮጵያ ሰአት አቆጣጠር ከቀኑ 11 ሰአት ከ30 ደቂቃ ላይ የመከላከያ ንብረት የሆነ ታርጋ ቁጥሩ “መከ 471 87” የሆነ ኦራል መኪና ከሶማሊ ክልል የተፈናቀሉ የኦሮሞ ተወላጆችን በመጫን ሃረር ከተማ ገብቷል። መከላከያ ጥበቃ ማድረግ ሲገባው ጭራሽ የተፈናቀሉ ዜጎችን ማመላለሱ አግራሞት እንደፈጠረበትም ተናግሯል። የተፈናቀሉ የኦሮሞ ተወላጆች በሶማሊ ልዩ ሃይል አባላት ከፍተኛ ድብደባ እንደተፈጸመባቸው ተናግረዋል። ተፈናቃዮች ምስራቅ ሃረርጌ ዞን ፖሊስ ጣቢያና ጅኔላ ፖሊስ ጣቢያ ውስጥ ተጠልለዋል።
በምስራቅ ሃረርጌ የሚገኙ ነዋሪዎች አገዛዙ የብሄር ግጭት ሊቀሰቀስ ይችላል በሚል ስጋታቸውን እየገለጹ ነው። በተለይ የሶማሊ ክልል መንግስት በኦሮሞ ህዝብ ተገድለዋል ብሎ የሚላቸውን የሶማሊ ተወላጆች በፊልም ቀርጾ ለማቅረብ እንቅስቃሴ የጀመረ ሲሆን፣ ፊልሙ ሆን ተብሎ የብሄር ግጭት ለመቀስቀስ የታቀደ ነው ሲሉ ጉዳዩን በቅርበት የሚከታተሉ ወገኖች ገልጸዋል። መሰረታዊው ችግር በአገዛዙና በህዝብ መካከል እንጅ በሁለቱ ብሄሮች መካከል አለመሆኑን የሚገልጹት እነዚህ ወገኖች፣ ፊልሞችን አቀናብሮ በማቅረብ የብሄር ግጭት ለመቀስቀስ የሚደረገው አደገኛ አካሄድ በጊዜ ካልቆመ ፣ መዘዙ ለሁሉም ይተርፋል በማለት ያስጠነቅቃሉ።
በሌላ በኩል ራሳቸውን ከሚሊሺያዎች ጥቃት ለመከላከል የታጠቁ የኦሮሞ ተወላጆች በመከላከያ ሰራዊት አማካንኝነት የጦር መሳሪያቸውን እንዲፈቱ እየተደረገ መሆኑን ከአካባቢው የሚደርሱን መረጃዎች ያመለክታሉ።
የክልሉ የኮሚኒኬሽን ሃላፊ አቶ ኢዲሪስ ኢስማኤል ከአሜሪካ ድምጽ ሬዲዮ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ የሶማሊ ልዩ ሃይል ጥቃት አለመፈጸሙን ገልጸው፣ ይህንንም የፌደራል መንግስት እና መከላከያ ከሶማሊ ክልል ከፍተኛ አመራሮች ጋር ባደረጉት ውይይት አረጋግጠዋል ብለዋል። ከዚህ በተቃራኒ ግን የኦሮምያ ክልል የኮሚኒኬሽን ቢሮ ሃላፊ አቶ አዲሱ አረጋ ወደ ኦሮምያ ክልል ዘልቆ በመግባት ጥቃት የሚፈጽመው የሶማሊ ልዩ ሃይል መሆኑን ማረጋገጫ አለን ብለዋል። የህዝብ ግንኙነት ሃላፊው እንዳሉት የፌደራል መንግስት ባለስልጣናትና የመከላከያ አዣዦች፣ የኦህዴድ ባለስልጣናትን በማግለል የሶማሊ ክልል መሪዎችን ብቻ አነጋግረው የሶማሊ ልዩ ሃይል በኦሮሞ ህዝብ ላይ ጥቃት አልፈጸመም ብለው ድምዳሜ ላይ ደርሰው ከሆነ፣ የፌደራል መንግስት ባለስልጣናትና የመከላከያ አዛዦች ከሶማሊ ክልል መሪዎች ጋር ያላቸውን የጠበቀ ግንኙነት ብቻ ሳይሆን፣ ከኦህዴድ ባለስልጣናት ጀርባ የሚሰሩት ስራ እንዳለ ያመለከታል በማለት ዘጋቢያችን አስተያየቱን አስፍሯል።

No comments:

Post a Comment