Thursday, September 21, 2017

በኦሮምያና በሶማሊ ክልል ድንበር ላይ ተኩስ እንደነበር ተገለጸ

(ኢሳት ዜና መስከረም 11 ቀን 2010ዓም) በኦሮምያና በሶማሊ ክልል ድንበር ላይ ተኩስ እንደነበር ተገለጸ
የኦሮምያና የሶማሊ ክልል መሪዎች የሰላም ስምምነት መፈራራቸውን ከገለጹ በሁዋላ አሁንም ግጭቶች አለመቆማቸውን ወኪላችን ዘግቧል።
ትናንት ጭናክሰን ወረዳ ቆቦ ላይ ከባድ ጦርነት መካሄዱን የአካባቢውን ባለስልጣናት ዋቢ በማድረግ የገለጸው ዘጋቢያችን፣ ግጭቱ በመባባሱ የምስራቅ እዝ አዛዡ ጄ/ል ማሾ በዬነ ወደ አካባቢው ለመጓዝ ተገዷል። ግጭቱ በሶማሊ ልዩ ሃይል አባላትና በህዝቡ መካከል የተካሄደ ነው። በግጭቱ ምን ያክል ሰዎች እንደተጎዱ ለማወቅ አልተቻለም። ለኢሳት የሚደርሱት መረጃዎች እንደሚያመለክቱት ግጭቱ እየተባባሰ ሊሄድ የሚችልበት ምልክቶች እየታዩ ነው። በሁለቱ ክልሎች መካከል የሰፈሩት የመከላከያ አባላት በኦሮሞ ተወላጆች ላይ ግልጽ አድልኦ በማድረግ አንዳንድ የኦሮሞ ተወላጆችን እየያዙ በማሰር ላይ ናቸው። 

በሌላ በኩል ከሶማሊ ክልል በጉልበት የተፈናቀሉትን የኦሮሞ ተወላጆች ወደ ትውልድ ቀያቸው በመውሰድ ለማስፈር እየተደረገ ያለው ጥረት እክል ገጥሞታል። ተፈናቃዮቹ እኛ ንብረታችንን ጥለን የመጣነው ሶማሊ ክልል ነው፣ መሄድ ካለብን ወደ መጣንበት ክልል እንጅ ወደ ትውልድ ቀያችን እንዴት እንሄዳለን በማለት ጥያቄ እየጠየቁ ነው። አንዳንድ ተፈናቃዮች ፣ አሁን ካለንበት ሁኔታ ይሻላል በሚል ወደ ተወለደቡት አካባቢዎች ያመሩ ሲሆን፣ ብዙዎቹ ግን “ መሬት የለንም፣ ሃብት የለንም፣ ቤተሰቦቻችንም እኛን ለመሸከም አይችሉም፣ ሃብትና ንብረታችንን ጥለን ወጥተናል ስለዚህ ወደ ትውልድ ቦታችን ብንመለስ ለችግር እንዳረጋለን እንጅ የምናገኘው ነገር የለም በሚል ለመሄድ ፈቃደኞች አለሆኑም።”
ተፈናቃዮችን ወደ ሶማሊ ክልል የመመለሱ ነገር ፍጹም የማይቻል ነው የሚለው ዘጋቢያችን አሁንም ድረስ እየተንጠባጠቡ ሃረር የሚገቡ ሰዎች መኖራቸውን ገልጿል።
በተያያዘ ዜናም ከሶስት ቀናት በፊት ተፈናቃዮችን ጭኖ ኮምቦልቻ አካባቢ ተገልብጦ በነበረው መኪና ህይወት ፋና ሆስፒታል ከገቡት ቁስለኞች መካከል አንዱ ትናንት ህይወቱ አልፏል። በዚሁ አደጋ የሞቱት ሰዎች ቁጥር 7 ደርሷል።

No comments:

Post a Comment