Friday, September 5, 2014

“በሽብር” ተከሶ ፍ/ቤት የቀረበው ወጣቱ ፖለቲከኛና መምህር አብርሃ ደስታ የጊዜ ቀጠሮ ተጠየቀበት

ፍኖተ ነፃነት ጋዜጣ

ወጣቱ መምህርና ፖለቲከኛ ዛሬ በግምት 9፡00 ሰዓት ፍርድ ቤት ቅጥር ግቢ ሲደርስ በግቢው የነበሩ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችና አባሎች እንዲሁም የአብርሃ ደስታ ደጋፊዎች በጭብጨባ ያላቸውን አክብሮት የገለጹለት ሲሆን እሱም አጸፋውን መልሷል፡፡ ከማዕከላዊ አጅበውት የመጡት የፌዴራል ፖሊሶች ለምን አጨበጨባችሁ እያንዳንዳችሁ ትገባላችሁ በማለት እያስፈራሩ ግቢውን ለቃችሁ ውጡ በማለት ከግቢ ለማስወጣት ሙከራ ያደረጉ ሲሆን ጉዳዩን ሊከታተል የመጣው ታዳሚም ለምን እንወጣለን አንወጣም እኛም ችሎት ተገኝተን ልንከታተል ሲገባ ግቢ ውስጥ መቆምም ልትከለክሉን ነው በማለት ተቃውሞ በማሰማቱ ችሎቱ እስኪጠናቀቅ በግቢው እንድንቆይ ተደረገ፡፡ የክሱ ጉዳይ የታየው በችሎት ሳይሆን በጽ/ቤት ነበር፣ ወጣቱ ፖለቲከኛ አብርሃ ደስታም ከጠበቃዬ ጋር ልገናኝ አልቻልኩም፣ ዘመድ አዝማድም ሊጠይቀኝ አልቻለም በማለት ለፍ/ቤቱ አስረድቷል፡፡

ዳኛውም ከጠበቃና ከቤተሰብ ጋር የማታገናኙ ከሆነ እርምጃ እወስዳለሁ በማለት ማሳሰቢያ ሰጥተዋል፡፡ ፖሊስ ተጨማሪ ማስረጃና ምስክር ለማሰባሰብ የጊዜ ቀጠሮ በመጠየቁ ተጨማሪ የጊዜ ቀጠሮውን ጠበቃ ተማም አባቡልጉ ተቃውመውታል ፖሊስ ደንበኛዬን ከመያዙ በፊት ማስረጃና ምስክሮችን ማዘጋጀት ነበረበት ነገር ግን አሁንም ደንበኛዬ ታስረው ማስረጃና ምስክር ሊባል አይገባም፣ እስራቱ ህገወጥ ነው በማለታቸው ዳኛው እንዳትሰራ አደርግሃለሁ ጥብቅናህን በፍትህ ሚ/ር አሳግድብሃለሁ በማለት እንዳስፈራሯቸው ለፍኖተ ነፃነት ገልፀዋል፡፡ በመጨረሻም ዳኛው ፖሊስ የጠየቀውን የጊዜ ቀጠሮው ፈቅደው ለመስከረም 22ቀን 2007 ዓ.ም ከቀኑ 8፡00 እንድትገኙ በማለት ችሎቱ ተጠናቋል፡፡ አብርሃ ከችሎቱ ሲወጣም የሱን ጉዳይ ሊከታተል የመጣው ታዳሚ በጭብጨባ ሸኝቶታል፡፡

No comments:

Post a Comment