Thursday, March 15, 2018

በኢትዮጵያ በተከሰተው የፖለቲካ ቀውስ ኬንያ በስደተኞች ልትጥለቀለቅ ትችላለች በማለት የኬንያ ምሁራን ስጋታቸውን ገለፁ።

(ኢሳት ዲሲ–መጋቢት 6/2010)በኢትዮጵያ በተከሰተው የፖለቲካ ቀውስ ኬንያ በስደተኞች ልትጥለቀለቅ ትችላለች በማለት የኬንያ ምሁራን ስጋታቸውን ገለፁ። በአዲስ አበባ ዙሪያ በየጎዳናው ሰዎች እየተገደሉ የአፍሪካ ሕብረት አዲስ አበባ ቁጭ ብሎ እስከመቼ ዝም ይላል ሲሉም ጠይቀዋል። የአፍሪካ ህብረት ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ጭምር ጥሪ በማቅረብ በኢትዮጵያ የተፈጠረውን ቀውስ ለማርገብ እንዲንቀሳቀስም ጠይቀዋል። ኢትዮጳያ የጭቆናው ሥረዓት ፍጻሜ ላይ ናት ሲሉም ተደምጠዋል። የኬኒያው NTV ቴሊቪዥን ትናንት ባዘጋጀው በዚህ ውይይት ላይ የአምነስቲ ኢንተርናሽናል የኬንያ ዳይሬክተርን ጨምሮ በውይይቱ የተሳተፉት ኬንያውያን ምሁራን በኢትዮጵያ ለረዥም ጊዜ የዘለቀው የዲሞክራሲ ዕጦት እና አምባገነናዊ አስተዳደር ዛሬ ሐገሪቱ ለገባችበት ቀውስ ምክንያት መሆኑን አብራርተዋል። ኢትዮጵያውያን ቤታቸውና የገበያ ቦታቸው ጭምር መገደያቸው እየሆነ በመምጣቱ ወደ ኬንያ ለመሰደድ ተገደዋል ያሉት የኬንያ ምሁራን ችግሩ መፍትሔ እንዲያገኝ የኬንያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርም የራሱን አስተዋፅኦ እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል። የኬንያው NTV ትናንት ናይሮቢ ላይ ያወያያቸው ኬንያውያን ባለሞያዎች የኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ እጅግ አሳሳቢነቱ ለኬንያውያንም የሚተርፍ መሆኑን አፅንኦት ሰጥተዋል። ኬንያ በስደተኛ ልትጥለቀለቅ ትችላለች በማለትም ሁሉም በጋራ ስጋታቸውን አንፀባርቀዋል። ከተወያዮቹ አንዱ የሆኑት ዶ/ር ሞሪንጋ እንደተናገሩት በአፍሪካ ቀንድ ፀጥታ ላይ ከሁለት ሳምንት በፊት በተካሄደ ውይይት የኢትዮጵያ ጉዳይ መነሳቱን አስታውሰዋል። የኢትዮጵያ ቀውስ ስለሚያስከትለው ውጤት የአካባቢው ሐገራት ምን ያህል ዝግጁ ናቸው የሚለውን አንስተን ተወያይተናል ያሉት ዶክተር ሞሪንጋ ጭቆና ስደትና ስርዓተ አልበኝነትን እንደሚያስከትል ገልጸዋል። ከሲቪሎች አልፎ የወታደሮችን ስደት ጭምር እንደሚያስከትልም አሳስበዋል። የሚሰደዱት ሁሉ
ተሰደው ለመቅረት ሳይሆን ተዘጋጅተው ተመልሰው ለመፋለም ጭምር መሆኑን በመዘርዘር ከኬንያ ፀጥታ አንፃር ጭምር ጉዳዩን ተመልክተዋል። በኢትዮጵያ ለ6 ወራት የሚዘልቅ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መ ታወጅንና የጠቅላይሚኒስትሩ የስልጣን የመልቀቅ ጥያቄን ጭምር በማንሳት፣ ስልጣን ላይ ያሉት ወገኖች ወዴት እንደሚሄዱ ተቸግረዋል ያሉት ኬኒያውያን ምሁራን የስልጣን መሸጋገሪያ ግልፅ መመሪያ ስላሌቸውም ውዥንብር ውስጥ ገብተዋል ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል። ኢትዮጵያ አሁን የምትገኝበት ሁኔታ የዲሞክራሲ መጀመሪያ ሳይሆን የፈላጭ ቆራጭ አገዛዝ ፍፃሜ ነው ያሉት ሌላው ተወያይ ዶክተር ሐሰን ካናንጆ ኢትዮጵያ ከንጉሱና ከደርግ በቀጠለ ፈላጭ ቆራጭ አገዛዝ ስር መቆየቷን አስታውሰዋል። በዚህ ረገድ ኬንያ የራሷን ሚና መጫወት እንዳለበትም አሳስበዋል። 50 ሚሊየን ኦሮሞ ተፈናቅሎ ቢመጣ ምን ልንሆን ነው ሲሉም ጠይቀዋል። ዝምታውን የምንሰብርበትና የምንንቀሳቀስበት ጊዜ አሁን ነው ሲሉም ለኬንያ መንግስት ጥሪ አቅርበዋል። በኬንያ ግማሽ ሚሊዮን ያህል የሶማሌ ስደተኞች ይኖራሉ፤ ከኢትዮጵያ ተጨማሪ 2 እና 3 ሚሊየን ስደተኛ ቢመጣስ በማለት የጠየቁትና ራሳችንን ለተጨማሪ ስደተኞች እናዘጋጅ በማለት ሌላኛው የውይይቱ ተሳታፊ አሳስበዋል። በኢትዮጵያ ያለው በመፈራረስ ላይ ያለ መንግስት ነው በማለት ስርዓቱን ፌይልድ ስቴት በማለት የገለፁት ኬንያዊ የዓለም አቀፉን ማህበረሰብ እንዲሁም፣ መቀመጫውን አዲስ አበባ ያደረገው የአፍሪካ ሕብረት ዝምታን ተችተዋል። በኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት እንዲከበርና ዲሞክራሲ ዕውን እንዲሆን ሚናቸውን አልተወጡም ሲሉ ተችተዋል። በአዲስ አበባ ዙሪያ በመንገድ ላይ ሰዎች እየተገደሉ የአፍሪካ ህብረት አዲስ አበባ ውስጥ ሆኖ ማንቀላፋትን መርጧል በማለት የተቹት ኬንያዊ ዳግም ሁኔታዎች ከመከሰታቸው በፊት ራሳችንን ማዘጋጀት አለብን ፣ስደተኞቹ ስለሚገቡበት ሁኔታ ከወዲሁ ስራዎች መሰራት አለባቸው ሲሉም አሳስበዋል። አሁን የሚያስፈልገው የኢትዮጵያን መንግስት ወደ ጠረጴዛ አምጥቶ በችግሮቹ ዙሪያ መፍትሄ እንዲፈልግ ማድረግ አይደለም ፣የሚያስፈልገው የአፍሪካ ሕብረት ከእንቅልፉ ነቅቶ በጉዳዩ ላይ አለም አቀፉን ማህበረሰብ እንዲያንቀሳቅስ ነው ሲሉ ጥሪያቸውን አቅርበዋል። የኬንያ 5 ምሁራን በሞያሌ የተከሰተው ግድያ ያስከተለውን ስደት መነሻ በማድረግ በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ NTV ላይ የተወያዩት ትናንት ረቡዕ መሆኑም ታውቋል።

No comments:

Post a Comment