Monday, March 19, 2018

አማራ ክልል የሚታየው የነዳጅ እጥረት የክልሉን ህዝብ ፈተና ውስጥ ከቶታል የዋጋ ንረቱም እያደር በመጨመር ላይ ነው

አማራ ክልል የሚታየው የነዳጅ እጥረት የክልሉን ህዝብ ፈተና ውስጥ ከቶታል የዋጋ ንረቱም እያደር በመጨመር ላይ ነው (ኢሳት ዜና ማጋቢት 10 ቀን 2010 ዓ/ም) በክልሉ የሚታዬው የነዳጅ እጥረት የህብረተሰቡን ኑሮ ማናጋት ጀምሯል። ነዳጅ ለማግኘት ለቀናት ወረፋ መያዝ ግድ እያለ ነው። በነዳጅ የሚሰሩ ፋብሪካዎች ስራ እያቆሙ ነው። የትራንስፖርት ዘርፉ በአጋጣመው የነዳጅ እጥረት የዋጋ ጭማሪ እያደረገ ነው። ይህን ተከትሎም የእቃዎች ዋጋ በአስደንጋጭ ሁኔታ እየጨመረ ነው። በክልሉ ያለው የነዳጅ አቅርቦት አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱን የኢትዮጵያ ነዳጅ አቅራቢ ድርጅት፣ ለክልሉ ነዳጅ የሚያቀርቡ ኩባንያዎችና በለማደያዎች በአንድ የምክክር መድረክ ላይ በአንድ ድምጽ ተናግረዋል። የአማራ ክልል የመገናኛ ብዙሃን በክልሉ የነዳጅ ፍላጐት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ የመጣ ቢሆንም፣ የነዳጅ አቅርቦቱና ስርጭቱን ግን አነስተኛ እና ኢ-ፍትሃዊ በመሆኑ ተሽከርካሪዎችና በነዳጅ የሚሰሩ ኢንዱስትሪዎች ብዙ ጊዜ ሥራ ለመፍታት መገደዳቸውን ይፋ አድርጓል። በክልሉ ለተፈጠረው የነዳጅ እጥረት በምክንያትነት የቀረቡት በክልሉ ያለው የነዳጅ ማጠራቀሚያ በደርግ ዘመን የተገነባ
መሆኑን ከዚያ በሁዋላ ሊገነባ አለመቻሉም፣ እንዲሁም የተለያዩ ቢሮክራሲያዊ ውጣውረዶችና ህገወጥ ንግድ በምክንያትነት ተጠቅሰዋል። ባለፈው ሳምንት የተጠራው የነዳጅ ማዕቀብ አድማ እንዲሁም በኢትዮጵያ የተነሳውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ ባጋጠመው የውጭ ምንዛሬ እጥረት የነዳጅ አቅርቦት እንዲስተጉዋጎል ማድረጉን በወይይቱ ላይ ለማንሳት የደፈረ አካል የለም። በመተማ አካባቢ በርካታ መኪኖች ነዳጅ ከሱዳን ማምጣት ሲገባቸው በፍራቻ መጓዝ አለመቻላቸውን የአካባቢው ነዋሪዎች ይናገራሉ። ይህም በክልሉ ለተፈጠረው የነዳጅ እጥረት አስተዋጽኦ ማድረጉ ይነገራል። በክልሉ የሚታዬው የዋጋ ንረት የህልውና ስጋት እንደደቀነባቸው ነዋሪዎች ይገልጻሉ። የእህል ዋጋ በከፍተኛ ደረጃ በመጨመሩ ሸማቾች በተለይም ቤተሰብ ያላቸው ዜጎች ፈተና ሆኖባቸዋል። በዳቦ ዋጋ ላይ እስከ 40 በመቶ ጭማሪ እየታዬ ሲሆን፣ በሌሎች እቃዎችም ላይ ተመሳሳይ ጭማሬ ታይቷል። የሸማቾች ጥበቃ ባለሥልጣን የዋጋ ንረቱ በሁሉም ክልሎች የሚታይ መሆኑን ገልጾ፣ ጭማሪ ባደረጉ ኩባንያዎች ላይ እርምጃ እንደሚወስድ አስታውቀዋል። ነጋዴዎች በበኩላቸው ለእቃዎች ዋጋ መናር ዋና ምክንያቱ የአቅርቦት እጥረት መሆኑን በመግለጽ፣ በተለይ ከውጭ የሚገቡ ነዳጅና እቃዎች ዋጋቸው የሚንረው ከምንዛሬ እጥረት አንጻር ነው ይላሉ።በዚህ ሁኔታ ውስጥ በነጋዴዎች ላይ የሚወሰደው እርምጃ “ ለነቀርሳ በሽታ ፓራሲታሞል እንደማዘዝ ነው” ይላሉ። በአገሪቱ ባሉ የተለያዩ የስራ ዘርፎች ከፍተኛ መቀዛቀዝ እየታየ ነው ፡፡

No comments:

Post a Comment