Tuesday, March 6, 2018

በኦሮምያና ጉራጌ ዞን የተጀመረው የስራ ማቆም አድማ ተጠናክሮ ቀጥሎአል

(ኢሳት ዜና የካቲት 27 ቀን 2010 ዓ/ም) የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን በመቃወም በኦሮምያ ክልል እና በጉራጌ ዞን የተጀመረው የስራ ማቆም አድማ ቀጥሏል። አድማው በኢኮኖሚው ላይ ከፍተኛ ቀውስ እየፈጠረ ነው። በአዲስ አበባ ዛሬም ያልተከፈቱ የንግድ ድርጅቶች መኖራቸውን የገለጹት ነዋሪዎች፣ በተለይ ከጠዋት ጀምረው ድርጅቶቻቸውን የሚዘጉና የሚከፍቱ ሰዎችን ለመሰለል ሰቪል ለብሰው ቁጥጥር ሲያደርጉ የዋሉት የደህንነት ሰራተኞች የተዘጉ የንግድ ድርጅቶችን ሲመዘግቡ ታይተዋል። የመንግስትም ሆነ የፋብሪካ ስራዎች ለሁለተኛ ቀን ተስተጓጉሎ ውሏል። በተለይ ከአዲስ አበባ በ20 ኪሜ ርቀት ላይ ስራቸውን የሚሰሩ ሰዎች በትራንስፖርት እጥረት ስራቸውን መስራት አለመቻላቸውን የደረሰን መረጃ ያመለክታል። በመሐል አ/አ ዙርያ እስከ 20 ኪሎ ሜትር በሚደርስ እርቀት ላይ ባሉ ከተሞች የሚሰሩ የመንግስት ሰራተኞችና ከዚሁ አካባቢ ተነሰተው ወደ መሐል የሚመጡ ነጋዴዎች ወደ መሐል አዲስ አበባ መግባት አልቻሉም። በአዲስ አበባ ዙሪያ ባሉ ከተሞች ሲሰሩ የነበሩ አሽከርካሪዎች የደህንነት ዋስትና እንደሚሰጣቸው ተገልጾ ስራ እንዲጀምሩ ወታደሮች ለማግባባት ሙከራ ቢያደርጉም ፣ ሾፌሮቹ
አሻፈረን በማለታቸው ሳይሳካላቸው ቀርቷል። በምስራቅ ሃርረጌ ዛሬም አድማው በተጠናከረ ሁኔታ የተጠናከረ ሲሆን፣ በተለይ በኮምቦልቻ በርካታ ወታደሮች ገብተው እንዲሰፍሩ ተደርጓል። በሃረር ደግሞ ነጋዴዎች ድርጅቶቻቸውን የማይከፍቱ ከሆነ እስከ 5 ዓመት በሚቆይ እስር እንደሚቀጡ ተነግሯቸዋል። በመቱ ከተማ በመካሄድ ላይ ያለውን አድማ ተከትሎ ወጣቶች በቀን ስራ ለሚተዳደሩና ለችግረኛ ቤተሰቦች የምሳ ግብዣ አድርገዋል። አድማው ያለ ምንም ችግር ሲካሄድ መዋሉን የአካባቢው ነዋሪዎች ገልጸዋል። በቡሌ ሆራ ትናንት የንግድ ድርጅቶቻቸውን ዘግተው የነበሩ ነጋዴዎች ዛሬ በጉልበት እንዲከፍቱ ተገደዋል። በሞያሌም እንዲሁ ትናንት በርካታ መኪኖች ቆመው የነበር ሲሆን፣ ወታደሮች በግድ ለማስከፈት ሙከራ አድርገዋል። በያቬሎ አድማው ዛሬም እንደቀጠለ ሲሆን፣ ወታደሮች አሁንም ለማስከፈት ሙከራ እያደረጉ ነው። በአካባቢው ያለው ውጥረት እንዳለ መሆኑን ነዋሪዎች ተናግረዋል። አድማው ከፍተኛ የኢኮኖሚ ጫና እየፈጠረ መሆኑንም የሚደርሱን መረጃዎች ያሳያሉ። በተለያዩ የደቡብ ክልል አካባቢዎች በተለይም በአዋሳ የምግብ ሸቀጦች ዋጋና የቤት ኪራይ ዋጋ እጥፍ በሚባል መልኩ ጨምሯል። ከአዋሳ ወደ አዲስ አበባ የሚደረገው ጉዞ በአየር ካልሆነ በመኪና ባለመቻሉ አብዛኞቹ ተጓዞች በከተማው ለመቆየት ተገደዋል። አውሮፕላን ለማግኘትም ከፍተኛ ወረፋ መጠበቅ ግድ ይላል ይላሉ። ወንዶ ገነት፣ ወንዶ ባሻ፣ ቱላ፣ አለታ ጩኮ ፣ ቦንሳ የተባሉ የደቡብ ክልል ወረዳዎች ዋና ገቢያቸው ጫት ሲሆን፣ የጫት ምርታቸውን ወደ ኦሮምያ ክልል እንደሚልኩና አሁን የንግድ እንቅስቃሴው በመቋረጡ ለከፍተኛ ችገር ተዳርገዋል። የምግብ ፍጆታ እቃ የሚገባው ከኦሮሚያ ክልል በመሆኑና እሱም በመቆሙ ንግዱ ላይ እና አከባቢው ላይ ከፍተኛ ጫና ማሳደሩን ነዋሪዎች ገልጸዋል።

No comments:

Post a Comment