Wednesday, November 8, 2017

ኢትዮጵያዊው አለምአቀፍ የልብ ህክምና ባለሙያ ያላቸው ዶክተር ፍቅሩ ማሩ ከእስር እንዲፈቱ አለምአቀፍ የፊርማ ማሰባሰብ ዘመቻ በመካሄድ ላይ መሆኑ ታወቀ።

 እስካሁንም በፊርማ ማሰባሰቡ ዘመቻ ከ112 ሺ በላይ ፊርማዎችን ማሰባሰብ መቻሉ ታውቋል። ለ40 አመታት በልብ ህክምናው ዘርፍ ከፍተኛ ልምድና እውቀት ያላቸው ኢትዮጵያዊው ዶክተር ፍቅሩ ማሩ በኢትዮጵያውያኑ 2000 ወደ ሀገራቸው በመግባት የልብ ህክምና መስጫ ተቋም አቋቁመው አገልግሎት መስጠት መጀመራቸው ይታወሳል። ዶክተር ፍቅሩ ከህክምና ባሻገር በዘርፉ ሌሎች ባለሙያዎችን ለማፍራት ስልጣና በመስጠትና የምርምር ጽሁፍ በማዘጋጀትም ይታወቃሉ። በተለይም በ3ኛው አለም ባሉ ሀገራት በመንቀሳቀስ የልብ ህክምና መሳሪያ በሌለባቸው ሀገራት መሳሪያ እንዲኖር ለማስቻል ከፍተኛ እንቅስቃሴ ሲያደርጉም ቆይተዋል። ትውልደ ኢትዮጵያዊ በመሆናቸውም የሀገራቸውን ህዝብ ለማገልገል ወደ ኢትዮጵያ የገቡት ዶክተር ፍቅሩ ይህ ነው ተብሎ ባልተጠቀሰ ምክንያት ከ2006 ጀምሮ ወደ እስር ቤት እንዲወረወሩ ተደርጓል።
ዶክተር ፍቅሩ ለእስር ከተዳረጉበት ከ2006 ጀምሮም ክስ ሳይመሰረትባቸውና ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ ሶስት አመታትን በእስር ቤት አሳልፈዋል። ከሶስት አመት እስር በኋላ በ2009 ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ የተደረጉት ዶክተር ፍቅሩ ከፖለቲካ ጋር ግንኙነት አለህ በሚል የተፈረደባቸውን የ4 አመት ከ8 ወር የእስር ቤት ቆይታ በተባለው ጊዜም አጠናቀዋል። በፍርድ ቤት የተወሰነባቸውን የእስራት ጊዜ አጠናቀው ከእስር ቤት ለመውጣት እየተዘጋጁ ባሉበት ጊዜ ግን በቂሊንጦ እስር ቤት ላይ በደረሰ ቃጠሎ ሳቢያ ከ37 ኢትዮጵያውያን ጋር ቃጠሎውን አስነስታችኋል በሚል ዳግም በእስር ቤት እንዲቆዩ ተደርጓል። ይሁንና እስር ቤቱ ተቃጠለ በተባለበት ወቅት ዶክተር ፍቅሩ በጠና ታመው ሆስፒታል እንደነበሩ የሚያሳዩ ማስረጃዎች በእጃቸውም ሆነ በእስር ቤቱ መዝገብ ላይ ይገኛል። ነገር ግን ማስረጃን መሰረት ያደረገ አሰራር በሌለበት የኢትዮጵያ የፍርድ ቤት አደኛኘት ምክንያት ዶክተር ፍቅሩ ያለምንም የህግ ማስረጃ በእስር ቤት በመሰቃየት ላይ ናቸው። ከህግ አግባብ ውጪ በእስር ቤት እየተሰቃዩ ያሉትን ታዋቂውን የልብ ህክምና ባለሙያ ዶክተር ፍቅሩ ማሩን ከእስር ማስለቀቅን አላማ ያደረገ የፊርማ ማሰባሰብ ስነስርአት በመካሄድ ላይ ነው። የዶክተር ፍቅሩ ማሩ ተማሪዎች፣የስራ ባልደረቦች እንዲሁም ወዳጆቻቸው በከፈቱት የፊርማ ማሰባሰብ ዘመቻ እስካሁን ከ112 ሺ በላይ ፊርማዎችን ማሰባሰብ ችለዋል። ይሰበሰባል ተብሎ የሚጠበቀው 120ሺ ፊርማ እንደሆነም ለማወቅ ተችሏል። በዶክተር ፍራንክ አሻር አማካኝነት በአውሮፓ የሚገኙ የህክምና ባለሙያዎች ተሳታፊ በሆኑበት በዚህ የፊርማ ማሰባሰብ ዘመቻ ላይ ሌሎች ኢትዮጵያውያንም ተሳትፎ እንዲያደርጉ ጥሪ ቀርቧል። ለ66 አመቱ አለምአቀፍ የህክምና ባለሙያ ስም በተከፈተው www.Freefikru.com በሚለው ድረ ገጽ ላይ በመግባት ፍርማን ማኖር እንደሚቻልም ተጠቅሷል። የፊርማ ማሰባሰቡ ዘመቻ ሲጠናቀቅም ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽሕፈት ቤትና ለፌደራሉ ዋና አቃቢ ህግ የሚቀርብ መሆኑ ታውቋል።

No comments:

Post a Comment