Friday, October 31, 2014

የግንቦት 7 በወታደራዊ፣ ፖለቲካዊ እና የመረጃ እና ደህንነት ትምህርቶች ያሰለጠናቸውን የመጨረሻው ታጋዮች ምርቃት አካሄደ

ኢሳት ዜና :-የግንቦት 7 ህዝባዊ ሃይል ለ 90 ቀናት በተከታታይ በወታደራዊ፣ ፖለቲካዊ እና የመረጃ እና ደህንነት ትምህርቶች ያሰለጠናቸውን ታጋዮች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እና የተለያዩ የተቃዋሚ ድርጅቶች ተወካዮች በተገኙበት በደመቀ  ሁኔታ ባስመረቀበት ወቅት የህዝባዊ ሃይሉ ስልጠና በግንቦት ሰባት ስም ከሚደረጉት ስልጠናዎች የመጨረሻው መሆኑ ተመልክቷል።

የህዝባዊ ሃይሉ ዋና አዛዥ ኮማንደር አሰፋ ማሩ ‘’ህዝባዊ  ሃይላችን በኢትዮጵያ ውስጥ የተንሰራፋውን ዘረኛና አፋኝ የወያኔ ስርዓት ከህዝብ እና ከሃገራችን ጫንቃ ላይ አስወግዶ በምትኩ ፍትሃዊና ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ለመገንባት ከተመሰረተ ጀምሮ ባለፉት ጊዚያት በርካታ ስራዎችን  በመስራት አስተማማኝ ድርጅታዊ አቋም ላይ ይገኛል’’ ማለታቸውን_ህዝባዊ ሃይሉ ለኢሳት የላከው መግለጫ ያመለክታል  ።

የኢትዮጲያ ህዝብ አርበኞች ግንባር፣ የአማራ ዴሞክራሲያዊ ሃይል ንቅናቄ እና  የግንቦት 7 የፍትህ፣ የነጻነትና የዴሞክራሲ ንቅናቄ ተዋህደው ባንድ ድርጅት ጥላ ስር ትግላቸውን አስተባብረው ለመታገል የሚያደርጉትን የውህደት ሂደት የመጨረሻ ምዕራፍ ላይ ባደረሱበት ወቅት ላይ መርቃቱ መደረጉን ያወደሱት ኮማንደሩ፣  የህዝባዊ ሃይሉ ስልጠና በግንቦት ሰባት ስም ከሚደረጉት ስልጠናዎች የመጨረሻው እንደሚሆን አስረግጠው ተናግረዋል።

ኮማንደሩ ‘’ስልጠና ለአንድ ታጋይ የትግሉ የመጀመሪያ ምዕራፍ እንደመሆኑ መጠን በስልጠና ላይ ያገኛችሁትን ትምህርት በተግባር ለቆምንለት ዓላማ  እና ተልዕኮ በቁርጠኝነት እንደምታውሉት ሙሉ እምነቴን እገልጻለሁ‘’ በማለት   ለስልጠናው መሳካት የተለያዩ  ድጋፎችን ላደረጉ አካላት ምስጋና  አቅርበዋል።

የግንቦት7 ህዝባዊ ሃይል ከዚህ ቀደም በ4ተከታታይ  ዙሮች  ያሰለጠናቸውን ታጋዮች ማስመረቁ ይታወሳል።


No comments:

Post a Comment