Sunday, October 19, 2014

ሁለቱ ሙሰኛ ባለስልጣናት /ከእየሩሳሌም አርአያ/

የትግራይ ክልል ፕሬዝዳንት አቶ አባይ ወልዱ ካስገነቧቸው ሁለት ቪላ ቤቶች አንዱን መሸጣቸውን ታማኝ ምንጮች አስታወቁ። የሕወሐት ሊቀመንበርና የትግራይ ክልል ፕሬዝዳንት የሆኑት አቶ አባይ ወልዱ በክልሉ ካስገነቧቸው ሁለት ቪላ ቤቶች አንዱ የሆነውና በመቀሌ – ዓዲ ሃውሲ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ የሚገኘውን ይህን ቪላ ከ9 ሚሊዮን ብር በላይ በሚገመት ወጪ ካስገነቡት በኋላ እንደሸጡት ማረጋገጥ የተቻለ ሲሆን ከዚህ በተጨማሪ አባይ ወልዱ በባለቤታቸው ወ/ሮ ትርፉ ኪዳነማርያም ስም በአዲግራት ከተማ ባለሶስት ፎቅ ዘመናዊና በውድ ዋጋ የተገነባ ቪላ እንዳላቸው ምንጮች አረጋግጠዋል። የአባይ ወልዱ ባለቤትና የህወሀት ማ/ኰሚቴ አባል እንዲሁም የፓርቲው የፕሮፖጋንዳ ሃላፊና የክልሉ ባለስልጣን የሆኑት ወ/ሮ ትርፉ ኪ/ማርያም በትግራይ ክልል ከመንገድና ኮንስትራክሽን ስራዎችና በተለያየ ንግድ በክልሉ ከተሰማሩ ነጋዴዎች ጋር ግንኙነት በመፍጠር በሙስና ተግባር መሰማራታቸውን ምንጮቹ አመልክተዋል። ..ይህ በእንዲህ እንዳለ የኦህዴድ ከፍተኛ አመራር አባልና በጅማ ክልል ባለስልጣን የነበረ አንድ ጎልማሳ እዚህ አሜሪካ ዋሽንግተን ዲሲ 4 የንግድ ድርጅቶች መክፈቱን ማረጋገጥ ተችሏል። ከነአባዱላ ገመዳ ጋር ጥብቅ ቁርኝት የነበረውና የ42 አመት ጐልማሳ የሆነው ይህ የኦሮሚያ- ጅማ ዞን የቀድሞ ባለስልጣን በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ይዞ አሜሪካ እንደገባና በአሁኑ ወቅት 1 ሊከር ስቶርና ሶስት 7/11 የንግድ መደብሮችን ከፍቶ እየሰራ መሆኑ ተረጋግጧል። 3 የተለያዩ ሃበሻ ወጣት ሴቶችን በማስቀመጥ ከ2ቱ የወለደው ይህ ግለሰብ ከኢትዮጵያ ምድር ዘርፎ ባመጣው ሃብት እንዳሻው እየፈነጨ መሆኑን የታዘቡ ወገኖች « በሰው ደም ሃብት አካብተው አሜሪካ የሚሸሸጉ ወንጀለኞችን የአገሪቱ መንግስት ለምን ዝም ይላቸዋል?..ለምን ሽፋን ይሰጣል?» ሲሉ በቁጭት መጠየቃቸው አልቀረም።


No comments:

Post a Comment