Saturday, November 1, 2014

ሕወሃት/ኢሕአዴግ ሕዝብ እንደማይመርጠው አውቋል – ግርማ ካሳ

ኦሮሞ ነን የሚሉ ኦነግ እየተባሉ በአሥር ሺሆች ታሰሩ። አማርኛ ተናጋሪውን፣ ጉራጌዉን፣ ጋሞዉን ፣ ወላያታውን ….ግንቦት ሰባት ናችሁ እያሉ ማጎር ቀጠሉ። የቀራቸው ትግሬው ነበር። በትግራይ የተነሳዉን ጠንካራ የዲሞክራሲና የለዉጥ ጥያቄ እየጨመረባቸው ሲመጣ፣ “ደሚት ናችሁ” በማለት፣ ይኸው የግፍ ዱላቸውን የትግራይ ተወላጆች ላይ ማሳረፍ ጀመረዋል።

ዛሬ አራት ወጣት ፖለቲከኞች፣ ሃብታሙ አያሌው፣ የሺዋስ አሰፋ ፣ ዳንኤል ሺበሺና አብርሃ ደስታ ሽብርተኞች ተብለው በኦፊሴል ክስ ተመስርቶባቸዋል። አምስት በመቶ ሊፈቱ ይችላሉ የሚል ግምት ነበረኝ። እንኳን ሊፈቱ ጭራሽ ሌሎች ስድስት ኢትዮጵያዉያን ተጨምረዋል። የአ/አ ዩኒቨርስቲ ማስትሬት ተማሪ የሆነው ወጣት ዘላለም ወርቅአገኘሁ፣ ዮናታን ወልዴ ፣ አብርሃም ሰለሞን ፣ ሰለሞን ግርማ ፣ ባህሩ ደጉና ተስፋዬ ተፈሪ ይባላሉ።


ሕወሃት/ኢሕአዴጎች ፣ የአምስት አመት የእድገትና ትራንስፎርሜሽ እቅድ በሚል፣ “ለሕዝብ የሚጠቅም ስራዎችን ሰርተን፣ ለምርጫ 2007፣ የሕዝብን ድጋፍ አናገኛለን” የሚል ተስፋ ነበራቸው። በርግጥም እቅዱ ግማሽ እንኳን ተሳክቶ ቢሆን እና የሕዝቡ የኢኮኖሚ ሁኔታ ትንሽ ቢሻሻል ኖሮ ፣ ኢሕአዴግ ድጋፍ የሚያገኝበት ሁኔታ ሊኖር ይችል ነበር። ነገር ግን እንዳሰቡት አልሄደላቸውም። እንኳን በተቀረው የአገሪቷ ግዛት፣ ጠንካራ በነበሩበት በትግራይ ሁሉ ሳይቀር ተቃዉሞ በጣም እየቀረበባቸው ነው። የኑሮ ዉድነቱ ከቁጥጥር ዉጭ ሆኗል። ባለፈው ምርጫ ዘጠን ሰባት 250 ብር የነበረው አንድ ኩንታል ጤፍ አሁን 2 ሺህ ብር ገብቷል። ኢሕአዴግ ስልጣን ሲይዝ አቶ መለስ በአሥር አመት ሁሉም ኢትዮጵያዊ በቀን ሶስቴ ይመገባል እንዳላሉ፣ ይኸው ከ23 አመታት በኋላ አብዛኛው ወገናችን በቀን አንዴ ነው የሚመገበው። ቁርስ፣ ምሳ ፣ ራት አንድ ላይ ፣ ቁምራ። ዉጭ አገር ዘመድ ያላቸውና ዶላር የሚላክላቸው ወይም በ ኤን.ጂ.ኦ የሚሰሩ አሊያም የስርዓቱ ተጠቃሚ ከሆኑት በቀር፣ በአሥር ሚሊዮኖች ለሚቆጠሩ፣ ኢትዮጵያ ሲኦል የሆነችበት ሁኔታ ነው ያለው። በመሆኑም ምርጫ ከተደረገ የሕዝቡን ድጋፍ እንደማያገኙ ገዢዎች እርግጠኞች ሆነዋል።

ስለዚህ በስልጣን ለመቆየት ያላቸው አማራጭ፣ ጠንካራ የሚሏቸውን ታጋዮች ማሰር፣ ጠንካራ የሚሏቸውን ድርጅቶች ማዳከምና ማሽመድመድ ነው።

ሃብታሙ አያሌው ከነሺመልስ ከማል ጋር በኢቲቪ ያደረገዉን ክርክር መቼም ሁላችንም የምናስታወሰው ነው። ያንን አይነት ክርክር መድገም አይፈልጉም። ሃብታሙ አያሌው አንድነትን ወክሎ በኢቲቪ ዲቤት እንደገና ቀረበ ማለት፣ ለነርሱ ራስ ምታት ነው። በመሆኑም እርሱን በእስር ቤት ማቆየቱን መረጡ።

አብርሃ ደስታ ሕውሃት የገነባዉን፣ በትግራይ ወንድሞቻችን እና በተቀረዉ ኢትዮጵያዊ መካከል የነበረዉን ግድግዳ ያፈራረሰ፣ ብዙ የማይታወቅ የነበረዉን በትግራይ የሚደረገዉን ግፍ ሲያጋልጥ የነበረ፣ ትግራይ፣ የሕወሃት ቤዝ ሳትሆን የዴሞክራሲና የፍትህ ደዉልና ድምጽ የሚሰማባት እንድትሆን ያደረገ ወጣት ነው። “ይህ ሰው አፉን ካልዘጋነው፣ ትግራይ አመለጠችን” በሚል መስለኝ ፣ ለምን የትግራይ ሕዝብ ችግር ተነገረ በሚል ፣ አብርሃ ደስታን አስሮ ማቆየቱን ወስነዋል።

የአንድነትን ፓርቲ አንዳንዶች፣ ካለማወቅም ይሁን ሆን ብለው፣ የ”አማሮች” እና የአዲስ አበባ ልሂቃን ፓርቲ አድርገው የሚወስዱ አሉ። ነገር ግን መረጃዎች እንደሚያሳዩት የአንድነት ፓርቲ ፣ በአማራዉ ክልል ካለው ድርጅታዊ ጥንካሬ በላይ፣ በደቡብ ክልል ያለው ድርጅታዊ ጥንካሬ እንደሚበልጥ ነው። በደቡብ ክልል የአንድነት ፓርቲ ቁልፍ ሰው ሆነው ሲንቀሳቀስ ከነበሩት መካከል፣ ወንድማችን ዳንኤል ሺበሺ አንዱና ዋናው ነው። ዳንኤልን ማሰር በደቡብ ያለውን እንቅስቃሴ ሊገታ ይችላል ብለው ስላሰቡ ይኸው ዳንኤልንም ለመፍታት አልፈለጉም።

ነገር ግን ከታሪክና ካለው ተጨባጭ ሁኔታ ትምህርት መዉሰድ ተሳናቸው እንጂ፣ ታጋዮችን በማሰር ትግሉን ማቆም አይቻልም። አብርሃ ደስታ ሲያደርግ እንደነበረው፣ በትግራይ የሚደረገዉን ግፍ የሚያጋልጡ እንደዉም በዝተዋል። እነ ሃብታሙና ዳንኤል ቢታሰሩም የአንድነት ፓርቲ በተጠናከረ ሁኔታ ድርጅታዊ መዋቅሩን እያሰፋ ለምርጫ 2007 እየተዘጋጀ ነው። የአንድነትን አቋም፣ የሕዝቡን ጥያቄ በተቀላጠፈ መልኩ የሚያስረዱ ብዙ ጠንካራ አባላት አሉት። እነ ሃብታሙ በመታሰራቸው የፓርቲውን ሥራ አላቆመውም። እንደዉም አዳዲስ አባላት እየመጡ፣ ያሉትም በሞራልና በስሜት በበለጠ ቁርጠኝነት እየሰሩ ነው። ለአገዛዙ ዉስጥ ዉስጡን ሲያገለግሉና ፓርቲውን ወደኋላ ለመጎተት የሚሞክሩትን፣ አንድነት እያራገፈ ግልጽነት ባለው መልኩ ምሪት እየሰጠ ነው።

ሕወሃት/ኢሕአዴጎች እንዳሰቡትና እንዳቀዱት በቀላሉ እነ አያለ ጫሚሶን ብቻ አሰልፈው፣ ሕዝቡ ግልፅ አማራጭ እንዳይቀርብለት አድርገው አይቀጥሉም። የአንድነት ፓርቲ፣ ጠንካራ አማራጭ ሆኖ፣ በሁሉም የአገሪቷ ክፍሎች ተወዳዳሪዎችን አሰልፎ፣ ሕዝቡ የሚያደርገዉንን ሰላማዊ የለውጥ እንቅስቃሴ ይመራል። አንድነት ትላንት እነ ብርቱካን ፣ አንዱዋለም ሲታሰሩ አልሞተም። ዛሬም እነ ሃብታሙ ሲታሰሩ አይሞትም። ነገም የሚታሰሩ ይኖራሉ። ትግሉ ግን አይቆምም !!!!


No comments:

Post a Comment