Tuesday, October 14, 2014

በሸኮ መዠንገር ታጣቂዎችና በፌደራል ፖሊሶች መካከል በተደረገው የተኩስ ልውውጥ ከ50 በላይ የፌደራልና የመከላከያ አባላት ተገደሉ

ኢሳት ዜና :-የአካባቢው ነዋሪዎች እንደሚሉት ባለፈው ቅዳሜና እሁድ የፌደራል ፖሊሶችን ልዩ ሃይልንና መከላከያን ባቀፈው የመንግስት ጦርና፣ መሳሪያ በታጠቁ የብሄረሰቡ ተወላጆች መካከል በተደረገው ውጊያ ከ40 በላይ የፌደራል ፖሊስ አባላትና
ከ10 ያላነሱ የመከላከያ ሰራዊት አባላት፣ 4 ታጣቂ ሚሊሺያዎችና 3 የወረዳ ፖሊሶች ተገድለዋል። የሟቾቹ አስከሬን በሚዛን አማን ሆስፒታል እንዲገባ ከተደረገ በሁዋላ፣ ዘመድ ያላቸው ወደ ዘመዶቻቸው ሲሸኙ፣ የቀሪዎቹ የቀብር ስነስርዓት ደግሞ ሚዛን ውስጥ መፈጸሙን ለማወቅ ተችሎአል።
በአዲስ አበባ የፖሊስ ሆስፒታል ምንጮች እንደገለጹት ከሆነ ደግሞ በርካታ አስከሬን ወደ ሆስፒታሉ የገባ ሲሆን፣ በመዠንገሮች የተገደሉት የፌደራል ፖሊስ አባላት እጅግ ከፍተኛ መሆኑን የሚያመለክት ነው።

በሸኮና መዠንገር ታጣቂዎች በኩል የደረሰውን ጉዳት ለማወቅ ባይቻልም፣ በዛሬው እለት መንግስት ተጨማሪ ሃይል ወደ አካባቢው በመላክ ጥቃት መፈጸሙንና ብዙዎችን መግደሉን የአይን እማኞች ገልጸዋል።
ከብሄረሰቡ ውጭ ያሉ ሰፋሪ ነዋሪዎች በሚደርስባቸው ጥቃት የተነሳ ቀያቸውን እየለቀቁ ሲሆን፣ ብዙዎቹም ለከፋ ችግር ተዳርገዋል።

በፌደራል ፖሊሶች ላይ የደረሰውን ጉዳት በሚዛን አማን ሆስፒታልተገኝቶ የተመለከተ አንድ ወጣት፣ ሁኔታው አስከፊና አስፈሪ መሆኑን ገልጿል።

በሌላ በኩል በአካባቢው ያለው የኢሳት ወኪል እንደገለጸው 18 የፌደራል ፖሊስ አስከሬን መቁጠሩን ተናግሯል። መንግስት ታንኮችንና ከባድ መሳሪያዎችን ማጓጓዙን ገልጾ፣ የሸኮ መዠንገር ተወላጆች ሚዛን ከተማ ድረስ በመምጣት ነዋሪዎች አካባቢውን ለቀው እንዲወጡ የሚያሳስብ
ወረቀት መበተናቸውንም ተናግሯል።በርካታ ቁጥር ያላቸው የተፈናቀሉ ኢትዮጵያን በሚዛን ከተማ ጎዳናዎች ላይ እንደሚታዩና እስካሁን እርዳታ ያደረገላቸው ድርጅት አለመኖሩንም ገልጿል።

መንግስት በጉዳዩ ላይ እስካሁን የሰጠው አስተያየት የለም። ከዚህ ቀደም በቴፒና ሜጤ በሚባሉት አካባቢዎች የነበረው ግጭት ወደ ጉራፈርዳ ወረዳ መሸጋገሩን እና የፌደራል ፖሊስ ወደ አካባቢው መሰማራቱን መዘገባችን ይታወሳል።
መስከረም አንድ በነበረው ግጭት መንግስት ከ 13 ያላነሱ ዜጎች መገደላቸውን ሲገልጽ፣ የአይን እማኞች የተገደሉትን ዜጎች ቁጥር ከ50 በላይ ያደርሱታል።


No comments:

Post a Comment