Friday, October 10, 2014

የጎዛምን ወረዳ የሰማያዊ አመራሮች በገዥው ፓርቲ አፈና እየተደረገባቸው መሆኑን አስታወቁ

‹‹ወጣትና አርሶ አደሩ ‹‹ለምን ከሰማያዊ አባላት ጋር ታወራላችሁ እየተባለ ይታሰራል››በምስራቅ ጎጃም ጎዛምን ወረዳ በአባሊባኖስ ቀበሌ የሰማያዊ ፓርቲ ቅርንጫፍ አመራሮችና አባላት፣ ‹‹ለምን የሰማያዊ ፓርቲ አባል ሆናችሁ?›› በሚል ከፍተኛ አፈና እየደረሰባቸው እንደሚገኝ ለነገረ ኢትዮጵያ ገለጹ፡፡
የወረዳው የፓርቲው አመራር የሆኑት አቶ አክሊሉ ውቤ፣ ወጣት ምህረት እንየውና አቶ አንመው ይዘንጋው ለነገረ ኢትዮጵያ እንደገለጹት የወረዳና የቀበሌ ባለስልጣናት የሰማያዊ አመራሮችን ከሰማያዊ ፓርቲ እንዲወጡ እንደሚያስገድዷቸው ገልጸዋል፡፡

አቶ አንመው ይዘዘው የተባለውን የፓርቲው አባል መስከረም 14/2007 ዓ.ም ከንጋቱ 12 ሰዓት ላይ ሚሊሻ ጥሩነህ መኮንን፣ ሚልሻ ሽታሁን ዘውዴ፣ ሚሊሻ አበባየሁ አባተ አስገድደው ወደ ቀበሌው ቢሮ በመውሰድ የቀበሌው ሊቀመንበር የሆኑት አቶ በልስቲ ትዛዜ ከሰማያዊ ፓርቲ ካልወጣ እንደሚገረፍ፣ ካልሆነ አገር ጥሎ መሰደድ እንዳለበት እንደዛቱበት ለማወቅ ተችሏል፡፡የቀበሌው ሊቀመንበር ‹‹ኢህአዴግ በ1997 ምርጫ ቢሸነፍም ሰራዊቱም፣ ወታደሩም፣ ፖሊሱም፣ የኛ ነው፣ እናንተ ወረቀትና እስክርቢቶ ይዛችሁ ልታሸንፉ አትችሉም፤ አሁንም እርምጃ እንወስድባችኋለን›› በሚል እንደዛቱበትና ከፓርቲው እንዲወጣ እንዳስጠነቀቁት ገልጾአል፡፡በተመሳሳይ አቶ አክሊሉ ውቤ የተባሉትን ግለሰብ ‹‹ቢያርፍ ይረፍ ከፖለቲካ ድርጅት መውጣት አለበት፣ ካላረፈ ለህይወቱ ያሰጋዋል›› በሚል የቀበሌው ሹም የሆኑት አቶ ገነነ እና አቶ በልስቲ ትዕዛዜ እንደዛቱባቸው ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ ምህረቱ ይታየው የተባለው ወጣትም ተመሳሳይ ማስፈራሪያ እንደደረሰበት ለማወቅ ተችሏል፡፡በሌላ በኩል አቶ በልስቲ ትዕዛዜ፣ ኮማንደር አንተነህ ፈንታሁን፣ አቶ ተሻገር አዲሱ የተባሉት የቀበሌው ባለስልጣናት ‹‹ከሰማያዊ ፓርቲ ጋር ለምን ታወራላችሁ፣ ለምን ከእነሱ ጋር ትቆማላችሁ›› በሚል በየዕለቱ ወጣቱንና አርሶ አደሩን እንደሚያስሩ የወረዳው የፓርቲው ቅርንጫፍ አመራሮች ለነገረ ኢትዮጵያ አክለው ገልጸዋል፡፡የሰማያዊ ፓርቲ የአደረጃጀት ጉዳይ ኃላፊ አቶ ብርሃኑ ተክለ ያሬድ ገዥው ፓርቲ ሰማያዊ ፓርቲ ቢሮ በከፈተባቸው ቦታዎች ቢሮዎችን ለመዝጋት፣ ቢሮ ለመክፈት እየጣረ በሚገኝባቸው ቦታዎች ደግሞ አባላቱንና አመራሮቹ ከፓርቲው እንዲወጡ ጫና እያደረገ እንደሚገኝ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ምንጭ ዘ-ሐበሻ

No comments:

Post a Comment