Friday, September 30, 2016

ፖሊስ የተመድ ሰራተኞች የእሬቻን በዓልን ለመከታተል ወደ ቢሾፍቱ እንዳይጓዙ አሳሰበ

ኢሳት (መስከረም 20 ፥ 2009)
የፊታችን ዕሁድ በደብረ ዘይት (ቢሾፍቱ) ከተማ የሚከበረውን የእሬቻ በዓል አከባባር ምክንያት በማድረግ የተባበሩት መንግስታት የደህንነትና የጸጥታ መምሪያ ሰራተኞች ወደ ከተማዋ እንዳይጓዙ አሳሰበ። 
መምሪያው ለሰራተኞቹ ባሰራጨው ማሳሰቢያ ተለይቶ የታወቀ የደህንነት ስጋት ባይኖርም፣ የድርጅቱ ሰራተኞች ቅዳሜ እኩለ ቀን ጀምሮ እስከ ሰኞ ድረስ የግል ጉዞን ጨምሮ ከማንኛውም እንቅስቃሴ እንዲታቀቡ ጠይቋል። 
በቅርቡ በኦሮሚያ ክልል ህዝባዊ ተቃውሞዎች ሲካሄዱ መሰንበታቸውን ያወሳው የተመድ የጸጥታና የደህንነት መምሪያ፣ የድርጅቱ ሰራተኞች ራሳቸውን ከማንኛውም ህዝባዊ ስብሰባዎች እንዲያርቁ አክሎ አሳስቧል። 
በክልሉ ለወራት የዘለቀውን ተቃውሞ ተከትሎ አዲስ አበባ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲን ጨምሮ የተለያዩ አለም አቀፍ ተቋማትና ኤምባሲዎች ሰራተኞቻቸው ወደ አካባቢው በሚያደርጉት ጉዞ ላይ የጥንቃቄ እርምጃን እንዲወስዱ ሲያሳስቡ መቆየታቸው ይታወሳል።

No comments:

Post a Comment