Wednesday, September 21, 2016

ጎንደር ቅዳሜ ገበያ ሱቆችን ለማቃጠል የተንቀሳቀሱ አራት ሰዎች በቁጥጥር ስር ዋሉ፥ ሌሎች ሱቆችን ለማቃጠል 50 ያክል ሰዎች እንደተሰማሩ ታውቋል።

ኢሳት (መስከረም 11 ፥ 2009)
በጎንደር ቅዳሜ ገበያ ያልተቃጠሉ ሱቆችን ለማቃጠል ቤንዚን ይዘው ሲንቀሳቀሱ የነበሩ አራት ሰዎች ረቡዕ በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ተከትሎ በጎንደር እንደገና ቁጣ ተቀሰቀሰ። ግለሰቦቹ ከትግራይ ክልል መላካቸውንም ለኢሳት መረጃ ያደረሱ ነዋሪዎች ተናግረዋል። 
ሱቆቹን ሲያቃጥሉ ሲሉ በነዋሪዎች ከተደረሰባቸው በኋላ በፖሊስ እጅ የገቡት አራቱ ግለሰቦች ወዲያውኑ ለፖሊስ በሰጡት መረጃ ለጥፋት ድርጊት የተላኩት እነሱን ጨምሮ 50 ያህል ሰዎች መሆናቸውንም እንዳስረዱም የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል። 
በግለሰቦቹ ድርጊት የተሳጩትና የቀድሞዎም ቃጠሎ በዚህ ሁኔታ እንደሆነ የተገነዘቡት የአራዳና የቅዳሜ ገበያ አካባቢ የጎንደር ነዋሪዎች በቁጣ አደባባይ ወጥተዋል።
በአካባቢው የሰፈረው የአጋዚ ክፍለጦር ታጣቂ ሃይል በነዋሪው ላይ እየተኮሰ መሆኑን ይህም ማምሻውን መቀጠሉን የኢሳት ምንጮች አብራርተዋል።
በርካታ ወጣቶች መታፈሳቸውም ተብራርቷል። ይህ ዘገባ እስከተጠናቀቀበት ጊዜ ድረስ የተኩስ ድምጽ ቀጥሏል።

No comments:

Post a Comment