Tuesday, May 19, 2015

መጭውን ምርጫ ተከትሎ በሰሜኑ የአገሪቱ ክፍል ከፍተኛ ውጥረት እየታየ ነው

ሚያዝያ ፲፩ (አስራ አንድ) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ለኢሳት የሚደርሱት መረጃዎች እንደሚያመለክቱት ከመጪው ምርጫ ጋር በተያያዘ በተለይ በሰሜን የአገሪቱ ክፍል አብዛኛው ህዝብ ረብሻ ይነሳል ብሎ ያምናል። በዚህም የተነሳ ቀድም ብለው ገንዘባቸውን ባንክ ያስቀመጡ ሰዎች ገንዘባቸውን እያወጡ ለምግብ የሚውሉ የእህል ዘሮችን፣ ጨውና ሌሎችንም እቃዎች እየገዙ ነው። ወፍጮ ቤቶች ሰሞኑን ተጨናንቀው ታይተዋል። አቅም ያለው ቤተሰብ ለሶስት ወር የሚበቃ እህል ሲያስፈጭ፣ ድሃው ደግሞ አቅሙ በፈቀደ መጠን ለማጠራቀም እየተሯሯጠ ነው።
“በየከተሞች የሚታየው የሰራዊት እንቅስቃሴና ጥበቃ በህዝቡ ውስጥ ተጨማሪ አለመረጋጋት እንዲፈጠር እያደረገ ነው” የሚለው ዘጋቢያችን፣ ” ህዝቡ መንግስት በከፍተኛ ሁከት እና ብጠብጥ ይወገዳል” የሚል ግምት ማሳደሩ አሁን ለሚታየው አለመረጋጋት ምክንያት ሳይሆን አልቀረም ይላል።
የኖርዌይ፣ ስዊድንና አሜሪካ ኢምባሲዎች ያወጡዋቸው መግለጫዎች ለአለመረጋጋቱ ተጨማሪ ምክንያት መሆናቸውን ይጠቅሳል።
በህዝቡ ብቻ ሳይሆን የመንግስት ባለስልጣናትም ተወጥረዋል። በየአካባቢው ሌሊቱን በውጠራ በተጠንቀቅ የሚያሳልፉ ወታደሮችን ማየት የተለመደ ክስተት ሆኗል።
በባህርዳር ከተማ የመከላከያን ዩኒፎርም የለበሱ ወታደሮች የመገናኛ ሬዲዮ፣ ከባድ መሳሪያና ሌሎችም ቁሳቁሶች በመያዝ በየቀኑ ከ11 ሰአት በሁዋላ በከተማይቱ የተለያዩ አቅጣጫዎች ይዞራሉ። ህዝቡ ማንኛውንም አመጽ በመሳሪያ እንቆጣጠራለን የሚል መልእክት ለማስተላለፍ ፈልገው ነው በማለት አስተያየት ይሰጣል።
በባህርዳር የመሰናዶ ተማሪዎች ለቅስቀሳ በተላከው የኢህአዴግ ቡድን ላይ ጥቃት የሰነዘሩ ሲሆን፣ ኢህአዴግ ይወረድ የሚል መፈክሮችን አሰምተዋል።
ባህርዳር፣ ጎንደር፣ አዋሳ፣ አዳማ፣ አምቦና አዲስ አበባ አመጽ ሊነሳባቸው ይችላል ተብሎ ከተለዩት ከተሞች መካከል ናቸው።
ገዢው ፓርቲ በተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ ወጣቶችን በስራና ስልጠና በመደለል እንዲሁም በረብሻ ስም እያፈሰ አዋሽ አርባ አካባቢ በሚገኝ በረሃማ ቦታ ወስዶ አስሮአቸዋል። በርካታ ወጣቶች ከእስር ቤት ሲያመልጡ መንገድ ላይ በአውሬ መበላታቸውን እንዲሁም በምግብና ውሃ ጥም መሞታቸውን የሚደረሱን ተከታታይ መረጃዎች ያመለክታሉ።
በቅርቡ ከማእከሉ ጠፍተው ጎንደር የደረሱ 5 ወጣቶች በእስር ቤቱ ያለው አስከፊ ሁኔታ እንዲጠፉ እንዳደረጋቸው ተናግረዋል። ብዙ ወጣቶች መንገድ ላይ ወድቀው ማየታቸውንም ተናግረዋል።
ከምርጫ ዜና ሳንወጣ የገዢው ፓርቲ ካድሬዎች የንብ ምልክት ያለበትን ፖስተር በየሰዎች ቤት ግድግዳ ላይ የሚለጥፉ ሲሆን፣ ፖስተሩ ተቀዶ ከተገኘ የቤቱ ባለቤት ተጠያቂ እየሆነ ነው። አንድ ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ አባት፣ “ንቧን እንዳይቀዷት ቁጭ ብየ ስጠብቅ አድራለሁ ” በማለት ያጋጠማቸውን ፈተና ተናግረዋል።


No comments:

Post a Comment