Saturday, May 24, 2014

በራችንን ከፍተን የወያኔን ሌብነት ማቆም አንችልም!


የወያኔ ጉጅሌና ሎሌዎቹ ስልጣናቸውን በህዝብ ፈቃድ ላይ እንዳልቆመ አሳምረው ያውቃሉ። ነጻ የህዝብ ምርጫ ቢኖር ምን እንደሚሆኑ የዛሬ ዘጠኝ አመት በአይናቸው አይተዋል፣ በጀሮቸው ሰምተዋል። ከዚያ ተመክሮ ተነስተው ዳግም የህዝብ ፈቃድ ላለመጠየቅ ምለዋል። ቅዱሱን የዴሞክራሲና የፍቅር መንገድ ሳይሆን ሳይጣናዊውን የከፋፍሎና አናክሶ የመግዛትን መንገድ ዋና ምርጫቸው አደርገው ከወሰዱ ሰንብተዋል። የፍትህና የዴሞክራሲ ሂደት በኢትዮጵያ እነሱ እስካሉ ድረስ እንዳይነሳ አድረገው ቀብረውታል። በራሳቸውና ጥቅማቸው ላይ ኮሽታ በመጣባቸው ቁጥር ችግሩ በምስኪኑና የነሱ ሰለባ በሆነው ህዝብ ውስጥ መካከል እንደተፈጠረ ግጭት ለማስመሰል እና ለማድረግ የማያደርጉት ነገር የለም።ወያኔ ሰሞኑን በመላው የኦሮሞ ተወላጆች የመጣበትን ተቃውሞ የአማራና የኦሮሞ ህዝቦች ጠብ ለማድረግ ያላደረገው ነገር የለም። መሰረታዊ የሆነውን የኦሮሞ ተማሪዎች ጥያቄ የባህርዳር እና በሌሎች የሀገሪቱ የሚገኙ ተማሪዎች ደግፈው ሂወታቸውን ያጡለትን የጋራ የወገንን ጥያቄ ለመቀልበስና፣ የኦሮሞና የአማራ ህዝብ ጠብ ለማድረግ ያላደረገው ጥረት የለም።መሰረታዊ የሆነውን የኦሮሞ ተማሪዎች ጥያቄ በጥይት ብቻ ሊመልሰው እንደማይችል የተረዳው ወያኔ፤ በግርግሩ ውስጥ አማሮችና ኦሮሞዎች ደም እንዲቃቡና እንዲጋጩ አድርጎ ገላጋይ ለመምሰል የሚያደርገው ሙከራ ባይሳካለትም ይህን ተንኮል በህዝቡ ውስጥ የመትከል አባዜ ስራውን በስፋት ተያይዞታል። ሰሞኑን በመላው ኦሮምያ ካድሬ በማሰማራትና ገላጋይ በመምሰል ዋናውን የወያኔ መሬት ዝርፊያ ይቁም የሚለውን ጥያቄ በማለባበስና በማፈን ዘዴ ላይ ይገኛል።ወያኔ ይህን ስልት የመረጠው ወያኔን የምንቃወም የነጻነትና የዴሞክራሲ አንድነት ሃይሎች የትብብር ደረጃ ያለበትን ሁኔታ ከግንዛቤ በማስገባት ነው።
በርግጥ ይህን ሳይጣናዊ በር የከፈትንለት እኛው የነፃነትና የዴሞክራሲ ሃይሎች ነን። በመካከላችን የተቀናጀና የተባበረ እንቅስቃሴ ማድረግ አለመቻላችን በብዙ መልኩም ህዝባችን የሚያስተባብር የጋራ አመራር በመጥፋቱ ነው።የወቅቱም ሆነ የዘላቂው ችግር መፍቻ ይህ የዴሞክራሲና የነጻነት ሃይሎች የተግባር ህብረትና ቅንጅት መሆኑን ለመማሪያ ከሰሞኑ ተሞክሯችን የበለጠ መማሪያ ያለ አይመስለንም። የወያኔ ጉልበት የተቃዋሚዎች ክፍፍል ብቻ ነው። እኛ ተጠቂዎቹ የችግሩን ማስወገጃና የዘላቂ የሀገራችንን ህይዎት የሚመራ የጋራ ራእይ አለማበጀታችን ነው። ሌባው ህዝባችንን የሚከፋፍልብን በራችንን በርግደን ስለከፈትን እና ለመከፋፈል ስለተመቸናቸው ነው። ይህን በር ከፍተን እስካቆየነው ድረስ የህዝባችን ደም በግፍ መፍሰሱ፣ ህዝባችን መዘረፉና በውርደት መኖሩ ይቀጥላል።ከወያኔ ፍትህም ሆነ የህዝባችን መሰረታዊ ችግር መፍትሄ አይጠበቅም። ከእባብ እንቁላል ርግብ መጠበቅ አይቻልምና።ግንቦት 7 የየፍትህ፣ የነጻነትና የዴሞክራሲ ንቅናቄ በኢትዮጵያ የአንዱ ብሄረሰብ ችግርየሚፈታው የሁላችንም ችግር ሲፈታ መሆኑን ያምናል። የተናጠል ትግላችን ከሚያስጠቃን በቀር ውጤት የለውም ብሎ ያምናል።በእኛ የግንቦት 7 አስተያየት የሰሞኑ የወያኔ ጭካኔና ደባ ከቁጭት ዘሎ የዘላቂ መፍትሄ መፈለጊያ እድል አድረገን ልንጠቀምበት ይገባል። ይህንና ተመሳሳይ ጥቃቶችን ተባብረን መመከት ባቃተን ቁጥር የህዝባችን መከራ እያራዘምን ነው። በዚህ ወቅት ህዝባችን ከአገራችን አጽናፍ እስከ አጽናፍ አንድ ድምጽ መሰማት መቻል ይኖርበታል። የሁላችንም አይን ያን ጊዜ ወያኔና ጉጅሌዎች ላይ ብቻ ይሆናል። ወያኔ የሚደግስልን የጎን ለጎን ግጭት ድግስ የሚከሽፈው ይህን ጊዜ ብቻ ነው።በሚደርሱን መረጃዎች መሰረት ወያኔ በተለይ በኦሮሞ ህዝብና በሌላው ብሄረሰቦች መካከል ስር የሰደደ ጠብ ለመፍጠር በመራወጥ ላይ ይገኛል።ለዚህ ተግባር የሚሆን የሰው፣ የገንዘብና የሚዲያ ሃይል አደራጅቷል። የተደገሰው የብሄር ለብሄር ግጭት ብቻ ሳይሆን በእያንዳንዱ ብሄረሰብ ውስጥ ክፍፍል በመፍጠር ህዝብ የማባላት ድግስ ነው። ወያኔ ለውጪ አሳዳሪዎች የህዝቡን ደም የማፈሰው የእርስ በእርስ ግጭት ለማስወገድ ነው የሚል መልስ በማዘጋጀት ላይ ይገኛል። ራሱ የሚያደርሰውን ጥፋት ሁሉ በተቃዋሚዎቹ እና በራሱ ህዝብ ውስጥ ባሉ ሰለባዎቹ ላይ ለማመካኘትና በዚሁ እብሪቱ ለመቀጠል መወሰኑን አረጋግጠናል።ግንቦት 7 ዘወትር እንደሚለው ሁሉ ህዝቡ የወያኔ የተንኮል መሳሪያ እንዳይሆን የልዩነት በሩን እንዲዘጋ የቻለውን ሁሉ ያደርጋል። ለሁሉም የነጻነትና ዴሞክራሲያዊ ሃይሎች የእንተባበር ጩኸቱንም ደግሞ ያሰማል።ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!!

No comments:

Post a Comment