Sunday, May 18, 2014

አኖሌ…..የባህር ዳር ነውር….አምቦ እና ግምቢ


ኢትዮጵያችን አደጋ ላይ ነች። የአደጋዋ ምንጭ ህወሃት እና ህወሃት ነው። ህወሃቶች በአገራችን ላይ የመዘዙት የበቀል ሰይፍ ወደ ሰገባው የሚመለስ አልሆነም። ከበቀል ስሜታቸው ጋር መቶ ዓመት የመንገስ ምኞት አላቸው። ምኞታቸውንም እውን ለማድረግ የንፁሃን ደም ለህወሃቶች መስዋዕት ሆኖ መቅረብ ይኖርበታል። እስከ ዛሬ ብዙ ኦሮሞዎችና አማሮች መሥዋዕት ሁነዋል። የመስዋዕቱ ምንጭ እንዳይደርቅ አሩሲ ላይ አኖሌ ቁሟል።እርሱን ተከትሎ ባህር ዳር “አማራና ኦሮሞ” ኳስ እንዲጫወቱ ሁኖ ነውር የሆኑ ስድቦች እየተነቀሱ ወጥተው በኢቲቭ እንዲተላለፍ ተደረገ። ይሄን ተከትሎ የመሬት ቅርምቱ ተከሰተ። አምቦና ግምቢ ላይ በህወሃት-ኦህዴድ ፊታውራሪነት የንፁሃን ደም በከንቱ ፈሰሶ ህወሃት የለመደውን ምሱን አገኘ።

ህወሃት የአኖሌ ሃውልት እንዲሰራ ሲፈቅድ የሚታየው በዚህ ሃውልት ምክንያት አብረው የኖሩ ህዝቦች ደም ተቃብተው በጠላትነት ሲቆሙ ነው።የአኖሌ ሃውልት በህወሃት-ኦህዴድ እጅ ሁኖ የሚሰብከው አብሮነትን ሳይሆን ልዩነትን ነው። ፍቅርን ሳይሆን ጥላቻን ነው። የአኖሌን ሃውልት የሚመስል ሌላ ሰማይ ጠቀስ ኃውልት በመቀሌ ከተማ ለትውልድ የሚተላለፍ ቂምን እየሰበከ ቁሟል። ስሙንም “የሰማዕታት” ሃውልት ብለው ይጠሩታል። ከአሩሲው አኖሌም ሆነ ከመቀሌው ሠማዕታት ሃውልት ትውልዱ የሚያተርፈው ቂም እና በቀል ነው። እነዚህ ሁለት ኃውልቶች ሠላምን አይሰብኩም፤ አብሮ መኖርን አያስተምሩም። ሃውሎቶቹን ያየ ግማሹ ቂም ይቋጥራል፤ ገሚሱ ይገረማል፤ ሌላውም የአገሪቱን መፃኢ ሁኔታ እያሰበ ይተክዛል። ህወሃቶች እጅግ ብዙ አሰቃቂ፤ አስገራሚ እና አሳዛኝ ነውሮችን በዚያች አገር ላይ መፈፀማቸው የታወቀ ነው።


የአኖሌ ኃውልት ተሠርቶ ከተመረቀ በኋላ በባህር ዳር ከተማ አማራና ኦሮሞ ኳስ እንዲጫወቱ ተደረገ። በዚያ ስቴዲየም ህወሃት-ብአዴን ያሰለጠኗቸው ምናምንቴ ካድሬዎች በኦሮሞዎቹ ላይ የስድብ ናዳ አወረዱ። ስድቡም በቀጥታ በቴሌቭዥን ለህዝቡ እንዲደርስ ሆነ። ይሄን ተመልክተው የሚቆጡ ሌሎች ምናምንቴዎች በህወሃት-ኦህዴዶች ተዘጋጅተው ወደ ህዝቡ መካከል ዘው ብለው ገቡ። የሚያቆማቸውም የመንግስት አካል አልተገኘም።

ይህ በእንዲህ እንዳለ በአዲስ አበባ “ልማት” ሰበብ በዙሪያዋ የሚገኙ ብዙ ገበሬዎች ተፈናቅለው ሜዳ ላይ ሊጣሉ የመሆናቸ ነገር ይናፈስ ጀመር።የሚነፍሰውን ወሬ መንግስት ነኝ የሚለው ቡድን ለህዝቡ ለማስረዳት ፈቃደኛ ሳይሆን በመቅረቱ ዜጎች ተቆጡ። ተማሪዎችም በየትምህት ክፍላቸው የገበሬዎችን ጥያቄ አንግበው ተነሱ። ”መሬት ላራሹ” እንደገና ዞሮ መጣ። ህወሃት ከማንም በላይ ለአርሶ አደሩ ቆሜያለው ቢልም እንደ ህወሃት አርሶ አደሩን መሬት አልባ ያደርገ ሥርዓት በኢትዮጵያ ታሪክ አልታየም። የአርሶ አደሩን መሬት ነጥቆ ለባዕዳን በመሸጥ እና አርሶ አደሩን ከነቤተሰቡ ሜዳ ላይ በመበተን ህወሃትን የሚመስለው እስከ ዛሬ አልታየም።

በየትምህርት ተቋማቱ ተማሪዎች ”ገበሬ ለምን ይፈናቀላል?” እያሉ መጠየቅ ጀመሩ። ከዚህ ፊትሃዊ ጥያቄ ጀርባ የአማራውን ህዝብ ስጋት ውስጥ የሚከት ነገር አብሮ ብቅ አለ።የገበሬዎች የመፈናቀል ጥያቄ ተረስቶ የተቃጠለው ‘የአማራ” ነው የተባለ ሆቴል የኢቲቪን መስኮት ያጨናንቀው ጀመር። በግምቢም የድሃ አማሮች ቤት እየተመረጠ በድንጋይ ይወቀር ጀመር። የንፁሃን አማሮች ደምም በከንቱ ፈሰሰ። እንዲህ ሲሆን ህወሃቶች ከቅጥረኛቸው ኦህዴድ ጋር የደም ፅዋቸውን አንስተው እየተጎነጩ በደስታ ሰከሩ።

የተከበራችሁ ያገራችን ዜጐች !

ከመቼውም ግዜ በከፋ ሁኔታ አገራችን አስቸጋሪ መንግድ ውስጥ ትገኛለች።በየቦታው በብሄሮች መካከል የሚነሳውን ግጭት የሚመራው ህወሃት መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል። ደጋግመን ለማለት እንደሞከርነው ህወሃት የህዝብ ጠላት መሆንን የመረጠ ቡድን ነው። ህወሃት ”አማራና ተፈጥሮ የትግራይ ህዝብ ቀንደኛ ጠላቶች ናቸው” ብሎ የሚያምን ቡድን ነው።በዋናነት የአማራን ህዝብ ለማጥፋት ባለፉት ሁለት አስርተ ዓመታት ሳይታክት ሠርቷል። አንድን ህዝብ እንደጠላት የቆጠረ ቡድን ለሌሎች የሰው ልጆች ወዳጅ እንዲሆን የሚያስችል የሞራል ግዴታ ይኖርዋል ለማለት አይቻልም።ስለዚህም ህወሃት የሰው ልጆች ሁሉ ጠላት ነው። ህወሃት ይሄ ነው ተብሎ የሚጠቀስ በጎ ታሪክ ያለው ድርጅት አይደለም። የህወሃት ታሪክ የግዲያ ታሪክ ነው። የህወሃት ታሪክ የዝሪፊያ ታሪክ ነው። የህወት ታሪክ የአገርን ክብር የማዋረድ ታሪክ ነው። ህወሃት ከዚህ የተለየ ታሪክ ያለው ቡድን አይደለም።

ውድ ኢትዮጵያዊያን !

አሁን ከእኛ ከፍ ያለ ትዕግስት፤ አስተዋይነት፤ አርቆ አሳቢነት ይጠበቃል። እኛ እንደ ህወሃቶች ርህራሄ የሌለን ጨካኞች መሆን አይኖርብንም።ህወሃቶች በዘረጉልን መረብ ውስጥ ገብተን እርስ በእርሳችን እንዳንተላለቅ ብርቱ ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርብናል። በአምቦ የሆነውን አይተናል።ከግምቢም አሳዛኝ ድምፅ ሰምተናል። ይሄ ግን የህዝብ ፍላጎት ሳይሆን የህወሃት-ኦህዴዶች እቅድ ነው። በባህር ዳር ስቴዲየም የተሰማው ነውረኛ ድምፅ የህዝብ ፍላጎት አይደለም። የህወሃት-ብ አዴኖች እጅ ሥራ ነው። ህወሃቶች በአማራውና በኦሮሞው መካከል የከረረ ግጭት አስነስተው በሚፈሰው የንፁሃን ዜጎች ደም እጃቸውን ታጠበው መቶ ዓመት ከነ ልጅ ልጆቻቸው ሊገዙን ይፈልጋሉ። ይሄ በሁሉም ዘንድ የሚታወቅ እውነት ነው። ይሄ ፍላጎታቻው እውን እንዳይሆን ፈጣሪን በመፍራት እና ለእውነት፤ ለፍትህ፤ለእኩልነት እና ለሁላችንም የምትሆን ኢትዮጵያን ለመፍጠር ዓይናችንን ከህወሃቶች ላይ ሳናነሳ በፅናት እንታገል።ኢትዮጵያችን ፈርጀ ብዙ ችግሮች ያሉባት አገር ነች። ከሁሉም ችግሯ የሚልቀው ግን ፍፁም ኃላፊነት የማይሰማቸው አገርን ለመምራት ግዙፍ የሆነ የሞራልም ሆነ የእውቀት ጉድለቶች ያሏቸው ህውሃቶች በአገራችን ጫንቃ ላይ ቁጢጢ ማለታቸው ነው። እነዚህ ቡድኖች አደብ ገዝተው ከህግ በታች መሆንን መልመድ ይኖርባቸዋል። እነርሱ ከህግ በላይ ሁነው ሌሎች ዜግች ከእነርሱ ሥር ሁነው የሚገኝ ልማትም ሆነ ሠላም የለም።

የተከበራችሁ የአገራችን ዜጎች !

ህወሃቶች ለርካሽ የፖለቲካ ጥቅም ሲሉ የሃውዜንን ህዝብ ማስጨፍጨፋቸው የቅርብ ግዜ ትዝታችን ነው። ዛሬም የሚያሰሉት እንዲህ ዓይነቱን ርካሽ ጥቅም ነው። በዚህ ግዜ እኔ ንፁህ ኦሮሞ ነኝ፤ እኔ ንፁህ አማራ ነኝ፤እኔ ከዚህ ነኝ እኔ ከዚያ ነኝ ማለት አይጠቅምም። እንዲህ ለማለት ግዜ አለው።ህወሃቶች የመጨረሻውን ካርድ መዘው ምድሪቷን በደም ሊያጨቀዩ ቆርጠው ተነስተዋል። በህዝቦች መካከል የሚነሳው ግጭትና የሚፈሰው ደም የህወሃቶችን የስልጣን ጥም ለማርካት የሚቀርብ መሥዋዕት ነው። የንፁሃን ዜጎች ደም በከንቱ እንዳይፈስ ከልዩነቶቻችን በላይ አንድ በሚያደርጉን ቁም ነገሮች ላይ እናተኩር። ዓይኖቻችን ልዩነቶቻችንን ለመጠፋፊያነት ለመጠቀም ከሚፈልጉት ህወሃቶች ላይ ሳናነሳ በአንድነት ለእኩልነት፤ ለነፃነት፤ለፍትህ እና ለሁላችንም የምትሆን አገር ለመፍጠር ሳናቅማማ እንታገል። ህወሃት እያለ ለሁላችንም የምትሆን አገር እንደማትኖር የታወቀ ነው።ለሁላችንም የምትሆን አገር እንድትፈጠር በየትኛውም መንገድ ህወሃት መወገድ ይኖርበታል።

አኖሌ…ባህር ዳር….አምቦና ግምቢ ላይ የሰማናቸው ድምፆች የጥፋት ድምፆች ናቸው። በዚህ ሁኔታ ለፈሰሰው ደም ተጠያቂው “መንግስት” ነኝ የሚለው ህወሃት-ኢህአዴግ ነው። የሌላ የማንም እጅ የለበትም። የንፁሃንን ህይወት ቀጥፎ በሠላም ስልጣን ላይ መቆየት ፈፅሞ አይቻልም። ህወሃት የብዙ የትግራይ ልጆችን መሠዋዕትነት ከንቱ ያስቀረ የጨካኞችና የነፍሰ ገዳዮች ስብስብ ሁኗል። ይሄን ነፍሰ ገዳይና ጨካኝ ቡድን ከተቆናጠጠበት ወንበር ላይ ለማውረድ ቆርጠን በምንችለው ሁሉ እየሠራን ነው። ዘወትር እንደምንለው ሁላችሁም በያላችሁበት፤ በምትችሉት መንገድ ሁሉ ለፍትህ፤ ለነፃነትና ለእኩልነት ዘብ የምትቆሙ ሁኑ እንጂ ህወሃቶች ባዘጋጁት የመተላለቂያ መርብ ውስጥ የምትወድቁ ደካሞች አትሁኑ።

ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ !




No comments:

Post a Comment