Thursday, May 24, 2018

መከላከያው ከእነ ጄ/ል ሳሞራ የኑስ እጅ እየወጣ ነው ተባለ

(ኢሳት ዜና ግንቦት 16 ቀን 2010 ዓ/ም) ወታደራዊ ምንጮች እንደሚገልጹት-አብዛኞቹ ከጄኔራልነት በታች ማዕረግ ያላቸው መኮንኖችና ወታደሮች ፣ጄ/ል ሳሞራ የኑስ የሚመራውን በ8 ጄኔራሎች የተዋቀረውን ወታደራዊ እዝ ለመቀበል ፍላጎት እያጡ ነው። የበታች መኮንኖችና ወታደሮች ለውጥ እየፈለጉ መምጣታቸውን የሚናገሩት ምንጮች፣ በዚህም ሳቢያ ቁንጮ ሹመኞቹ ትዕዛዞችን እንደ ወትሮው ማስፈጸም እየተቸገሩ ነው ይላሉ። ለውጡ ወታደራዊ ተቋማቱንም እንዲነካ የሚጠይቁት ወታደሮችና መኮንኖች፣ በቅርቡ አዲሱ ጠ/ሚኒስትር መከላከያውን የማዋቀር ዘመቻ ካላደረጉ በመከላከያው ውስጥ ከፍተኛ ተቃውሞ ሊነሳ ይችላል ሲሉ ያስጠነቅቃሉ። በሳሞራና በህወሃት ወታደራዊ አዛዦች እንደተማረሩ የሚናገሩት የሰራዊቱ አባላት፣ በሰራዊቱ ውስጥ አጠቃላይ መዋቅራዊ ለውጥ ይመጣል ብለው ተስፋ እያደረጉ መሆናቸውን አልሸሸጉም። መዋቅራዊ ለውጡ ሁሉንም አካባቢዎች ፍትሃዊ በሆነ መልኩ ያስተናግዳል ብለው እየጠበቁ እንደሆነም ገልጸዋል። “ በህዝቡ ላይ እርምጃ ውሰዱ ፣ ሽብርተኞች እና ገንጣዮች ገብተዋል እየተባልን እርምጃ እንድንወስድ ስንታዘዝ የአገር አንድነትን
የምናስጠብቅ ይመስለን ነበር” የሚሉት ወታደሮች፣ ዶ/ር አብይ የችግሩ መንስኤ የመንግስት ፖሊሲ መሆኑን በመገናኛ ብዙሃን ደጋግመው መናገራቸው፣ በአዛዦቻቸው ተታልለው በህዝባቸው ላይ በወሰዱት እርምጃ እንዲጸጸቱ እንዳደረጋቸው ይናገራሉ። አክለውም፦”ከዚህ በሁዋላ በእነ ሳሞራ የኑስ የመመራት ፍላጎት የለንም” ብለዋል። ይህ አስተያየት በሁሉም የሰራዊት አባላት ዘንድ ሰርጿል ወይ? በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ መኮንኖቹ ሲመልሱ “ አብዛኛው ወታደር ትዕዛዝ ለመቀበል ፍላጎት የለውም፣ በሳሞራም ሆነ በነባር ወታደራዊ አዛዦች መመራትን አይፈልግም፤ ይህን ደግሞ ወታደራዊ አዛዦች አውቀውታል። ስለዚህ በፍጥነት መዋቅራዊ ለውጥ ካልተደረገ ወታደሩ የራሱን እርምጃ ለመውሰድ ሊገደድ ይችላል፡” ብለዋል።

No comments:

Post a Comment