Wednesday, May 30, 2018

በኢህአዴግ አባል ድርጅቶች መካከል ያለው ልዩነት እየሰፋ ነው

 (ኢሳት ዜና ግንቦት 22 ቀን 2010 ዓ/ም) በኢትዮጵያ የሚካሄደውን የለውጥ እንቅስቃሴ ለማፈን ነባር የብአዴን እና የህወሃት አባላት በሙሉ ሃይላቸው እየተንቀሳቀሱ ነው። ለውጥ የሚፈልጉ የኢህአዴግ አባላት ቁጥራቸው እየጨመረ ቢሆንም፣ ነባር የኢህአዴግ አመራሮች ከአዲሶቹ የድርጅቱ አመራሮች ጋር ተስማምተው ለመጓዝ ተቸግረዋል። ህወሃት በብአዴን ውስጥ ያለውን ክፍፍል ለራሱ ጥቅም ለማዋል እየተንቀሳቀ ሲሆን በተለይ የለውጡን እንቅስቃሴ አይደግፉም የሚባሉትን ነባር የድርጅቱን አመራሮችና አንዳንድ ወጣት አመራሮችን በመያዝ፣ ለውጡን ለመቀልበስ እየሰራ ነው። በብአዴን ውስጥ የለውጡ እንቅስቃሴ አገራዊ በሆነና የህዝቡን ፍላጎት በሚያሟላ መንገድ እንዲቀጥል የሚፈልጉ ቡድኖች እየጎለበቱ ቢመጡም፣ አቶ በረከት ስምዖን፣ ህላዊ ዮሴፍ፣ ከበደ ጫኔና የመሳሰሉ ነባር አመራሮች የለውጡን እንቅስቃሴ ለመቀልበስ ከህወሃት ጎን ተሰልፈው ስራዎችን እየሰሩ ነው። የህወሃት መሪዎች ከደህዴን የተወሰኑ አመራሮችን ከጎናቸው ማሰልፍ ቢችሉም በኦህዴድ በኩል የሚከተሉዋቸውን ሰዎች ማግኘት አለመቻላቸው እንዲሁም በርካታ የብአዴን ወጣት አመራሮች የህወሃትን ሴራ ቀድሞ በመገንዘብ ለመተባባር ፈቃደኛ ባለመሆናቸው ህወሃት እንደልቡ መንቀሳቀስ አልቻለም። ለውጥ ፈላጊ የብአዴን አመራሮች የእነ በረከትን ፍላጎት ለማስፈጸም ፈቃደኛ አለመሆናቸው እነ አቶ በረከት የመጨረሻ የሚሉትን እድላቸውን ለመጠቀም ላይ ታች እያሉ መሆኑን ምንጮች ይናገራሉ። በድርጅቶች ውስጥ ያለው የሃሳብ ልዩነት እየሰፋ መሄዱ ኢህአዴግን ከ2 ሊከፍለው ይችላል ተብሏል። ጠ/ሚኒስትር አብይ አህመድ በለውጥ ፈላጊዎች እንጅ በነባር አመራሮች ዘንድ ድጋፍ የላቸውም። አንዳንድ ነባር አመራሮችን በጡረታ አሰናብተው የግል ስራ እየፈለጉ እንዲቀጠሩ ለሌሎች ደግሞ በቦርድ አባልነት እየሾሙ የግል ህይወታቸውን እንዲመሩ ለማድረግ ቢሞክሩም፣ ነባር አመራሮች ግን ከአመራር ቦታ መገለላቸውን በጸጋ አልተቀበሉትም። ህወሃት በመከላከያው እና ደህንነቱ ያለው የበላይነት እንዳይነካበት ጥረት እያደረገ ነው።

No comments:

Post a Comment