Thursday, February 1, 2018

የአማራ ክልላዊ መንግስት ንብረት ላይ ጉዳት ባደረሱ ግለሰቦች ላይ ርምጃ ሊወስድ መሆኑን አስታወቀ።

የክልሉ ፖሊስ ረዳት ኮሚሽነር በሰጡት መግለጫም ንብረት ላይ ጥፋት የፈጸሙ ሰዎችን ለመያዝ ክትትል እየተደረገ ነው ብለዋል። በወልዲያ፣መርሳና ቆቦ የተገደሉትን ሰላማዊ ዜጎችን በተመለከተ ግን ለህግ የሚቀርብ አካል ስለመኖሩ የተገለጸ ነገር የለም። ማንነትን መነሻ ያደረገ ጥቃት ተፈጽሟል በማለት የተሰጠው መግለጫ ብዙዎችን ማስቆጣቱ ተሰምቷል። የአማራ ክልል መንግስት ያወጣውን ይህን መግለጫ በሀገር ውስጥና በውጭ የሚንቀሳቀሱ የትግራይ መገናኛ ብዙሃን በምስጋና ተቀብለውታል። ክልሉን የሚያስተዳድረው የብሄረ አማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ ብአዴን ያወጣው መግለጫ ለአንድ ወገን ያደላ፣ በግፍ የተገደሉ ሰዎችን በመተው ለንብረት ውድመት ትኩረት የሰጠ እንደሆነ መረዳት ተችሏል። የህዝቡን ተቃውሞና በቁጣ የወሰደውን ርምጃ ሁከትና ስርዓት አልበኝነት በሚል የገለጸው የክልሉ መንግስት መግለጫ አንዳንዶቹ ማንነትን እየለዩ ጥቃት የሚሰነዘርባቸው መሆናቸውና ዜጐች ለዘመናት ያፈሩት ሀብትና ንብረት በአጭር ጊዜ መውደሙ በምንም መንገድ የክልሉንም ሆነ ችግሩ የተከሰተባቸውን አካባቢ ህዝቦች የማይወክል ተግባር ነው ሲል ኮንኖታል። መግለጫው ማንነትን ሲል በግልጽ ማንን እንደሆነ ያላሰፈረ ከመሆኑም በላይ በንብረቶቻቸው ላይ ጥቃት የተፈጸመባቸው ድርጅቶችና ግለሰቦች ከማንነት ይልቅ
በተሰለፉበት የፖለቲካ መስመር ከአገዛዙ ጋር በጥቅም የተቆራኙትን በመለየት መሆኑን መረጃዎችንና እማኞችን በመጥቀስ ኢሳት በተደጋጋሚ መዘገቡ ይታወሳል። ለአብነትም በመርሳ የፍርድ ቤት ዳኛ እንዲሁም በቆቦ የዘለቀ የእርሻ ሚካናይዜሽን ላይ የተወሰደው ርምጃ ከአገዛዙ ጋር ባለ ቁርኝት ተለይተው መሆኑን ማስታወስ ተችሏል። የትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪ ግንባር ህወሃት በሰሜን ወሎ የተከሰተውን የህዝብ ተቃውሞ በትግራይ ህዝብ ላይ የተነጣጠረ ጥቃት በማለት ድጋፍ ለማሰባሰብ የተጠቀመበትን የፕሮፖጋንዳ ቅስቀሳ የአማራ ክልል መንግስት እንዳለ አስተጋብቶታል ሲሉ አስተያየታቸውን የሰጡን የፖለቲካ ምሁራን ገልጸዋል። በትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪ ግንባር ወታደሮች በጥይት የተገደሉትን ከ30 በላይ ንጹሃንን በተመለከተ ከሀዘን መግለጫ በቀር ገዳዮቹን ለፍርድ ለማቅረብ የሚወሰድ ርምጃ ስለመኖሩ አልተጠቀሰም። ከወልዲያና መርሳ ከ500 በላይ ወጣቶች አፋር ጭፍራ ተወስደው በሚሰቃዩበት በዚህን ወቅት የክልሉ መንግስት ያሰራቸው የፌደራሉ መንግስት ነው የሚል ምላሽ መስጠቱን የሚገልጹት የፖለቲካ ምሁራን ክልሉን የሚያስተዳድረው የብአዴን አመራር ሙሉ በሙሉ በትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪ ግንባር ቁጥጥር ስር መውደቁን የሚያረጋግጥ ነው ይሉታል። የአማራውን ህዝብ ለተጨማሪ የጭቆና ዘመን መንገዱን እያመቻቸ ያለው ብአዴን ሌላ ታሪካዊ ጥፋት በዛሬው መግለጫው ፈጽሟል ሲሉም ይገልጻሉ። የሰሜን ወሎና ከሚሴ ሀገረ ስብከት ረዳት ሊቀ ጳጳስ የሆኑት ብጹእ አቡነ ኤርሚያስ በጥምቀት በዓል የተጨፈጨፉትን በተመለከተ የሰጡት መግለጫ ላይ የስርዓቱ ወታደሮችን ተጠያቂ ባደረጉበት ሁኔታ የአማራ ክልል መንግስት ተጎጂዎች ላይ ጣቱን መቀሰሩ ብዙዎች አስቆጥቷል። የክልሉ ፖሊስ ረዳት ኮሚሽነር በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫም በአገዛዙ በደልና ጭቆና የደረሰባቸውን ተጠያቂ በማድረግ የማደን ስራ መጀመሩን መግለጻቸው ታውቋል። የአማራ ክልል መንግስት ተበዳዩን ተጠያቂ በማድረግ ያወጣው መግለጫ የትግራይ የመገናኛ ብዙሃን በደስታ ተቀብለውታል። በውጭና በሀገር ውስጥ የሚገኙት የትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪ ግንባር ህወሃት ደጋፊ መገናኛ ብዙሃን ደስታቸውን ከምስጋና ጋር ለአማራ ክልል መንግስት ማስተላለፋቸው ታውቋል።

No comments:

Post a Comment