Thursday, February 1, 2018

በአዳማ ዛሬ የተቃውሞ ሰልፍ መደረጉ ተገለጸ።

 ህገወጥ ቤት ለማፍረስ የተጀመረውን እንቅስቃሴ በመቃወም በተደረገው ተቃውሞ ከፖሊስ ጋር ግጭት ተፈጥሮ በርካታ ሰዎች መጎዳታቸው ታውቋል። መንገዶች በድንጋይና በእንጨት ተዘግተው እንደነበር የጠቀሱት የኢሳት ምንጮች ወደ አመጽ የተቀየረውን የህዝቡን ተቃውሞ ለማስቆም የፖሊስ ሃይል ቁጥሩን ጨምሮ መሰማራቱን ገልጸዋል። በርካታ ሰዎች መታሰራቸውም ታውቋል። በአዳማ/ ናዝሬት ዛሬ የተካሄደው የተቃውሞ ሰልፍ መነሻ ህገወጥ ቤት ለማፍረስ በከተማዋ አስተዳደር እየተወሰደ ያለውን ርምጃ ለማስቆም ያለመ ነበር። ከሁለት ወራት በፊት በተመሳሳይ በተካሄደው ተቃውሞ የሰው ህይወት መጥፋቱ የሚታወስ ነው። ቤት አጥተው ከፍተኛ ችግር ውስጥ የገቡ ዜጎች መሬት በመግዛት የመኖሪያ ቤት ግንባታ ሲያከናውኑና ውሃና መብራትን ጨምሮ የተለያዩ የመሰረተ ልማት ዝርጋታዎች ሲከናወኑ አቁሙ ያላቸው አካል የለም። እስከ መጨረሻው በዝምታ የቆየው የከተማው አስተዳደርም ከዓመታት በኋላ ያለተለዋጭ ቦታና ቤት በላያችን ላይ ቤት እንዲፈርስ መወሰኑ
ኢሰብዓዊ ተግባር ነው በማለት ተቃውሞ ያሰሙት ሰልፈኞች ከፖሊስ ጋር መጋጨታቸውን የዓይን እማኞች ገልጸዋል። ጠዋት ላይ የተኩስ ድምጽ ይሰማ እንደነበርም ያገኘነው መረጃ አመልክቷል። ቤታችን አይፈርስም በሚል ተቃውሞ ማሰማት የጀመሩትን ነዋሪዎች ለመበተን የአገዛዙ ታጣቂዎች አስለቃሽ ጭስ የተጠቀሙ ቢሆንም የሰልፈኞቹ ቁጣ በማየሉ ወደ ሃይል ርምጃ መግባቱ ታውቋል። ተጨማሪ ሰራዊት ተሰማርቶ የነበረ ሲሆን መንገዶች በድንጋይና በእንጨት በመዘጋታቸው ለፖሊስ አስቸጋሪ ሁኔታን መፍጠሩን ለማወቅ ተችሏል። ከዚህ ቀደም ተደርጎ ከነበረው በበለጠ ጠንካራ የህዝብ ተቃውሞ በተሰማበት በዛሬው ሰልፍ ነዋሪው ቤታችንን ከማፍረሳችሁ በፊት እኛን ግደሉን በሚል ቁጣ ከፖሊስ ጋር ግብግብ የገጠመበት እንደሆነም ከዓይን እማኞች ምስክርነት ለመረዳት ተችሏል። ግጭቱ ወደ አመጽ በመሸጋገሩ ፖሊስም የሃይል ርምጃ በመውሰድ በርካታ ሰዎች ሊጎዱ መቻላቸውን ነው የደረሰን መረጃ የሚያመለክተው። አንዳንድ መረጃዎች የሰው ህይወት የጠፋ መሆኑን ቢገልጹም ኢሳት ግን ማረጋጋጥ አልቻለም። በተቃውሞው በርካታ ሰዎች ተጎድተው ወደ ሆስፒታል መወሰዳቸውም ታውቋል። አዳማን መሀል ለመሀል ሰንጥቆ የሚያልፈው ዋና የአስፋልት መንገድ ላይ የተካሄደው ተቃውሞ ወደሌሎች በአካባቢው የሚገኙትን የንግድ ቦታዎች ለሰዓታት እንዲዘጉ ማድረጉም ተጠቅሷል። ለጊዜው ቁጥራቸው ያልታወቁ ወጣቶች ታፍሰው መወሰዳቸውንም የደረሰን መረጃ አመልክቷል።

No comments:

Post a Comment