Tuesday, February 20, 2018

ወጣት ንግስት ይርጋን ጨምሮ የተወሰኑ እስረኞች ክሳቸው ተቋርጦ ተፈቱ

Image may contain: 1 person, smiling, standingሰሜን ጎንደር ተጀምሮ በአማራ ክልል የተቀጣጠለውን ህዝባዊ ተቃውሞ ፊት ሆነው ከመሩትና ካስተባበሩት መካከል በግንባር ቀደምነት የምትጠራዋ ወ/ት ንግስት ይርጋ ከሷ ተቋርጦ ከእስር ቤት ወጥታለች። በሽብር ወንጀል የተከሰሰችው ወ/ት ንግስት ከጎንደር ወደ አዲስ አበባ ማእከላዊ እስር ቤት በተዘዋወረችበት ወቅት ከፍተኛ የሆነ ሰብአዊ መብት ጥሰት ተፈጽሞባታል።ወ/ት ንግስት በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ እስር ቤት በቀዝቃዛና በጨለማ ክፍል ውስጥ ለረጅም ቀናት ታስራለች፣ ያለማንም ጠያቂ፣ ያለችበት ሁኔታ ሳይታወቅ ታፍና ለሳምንታት እንድትቆይ ተደርጋለች፣ ማታ ለምርመራ በሚል ከታሰረችበት ክፍል እየወጣች ሰብዓዊ ክብሯን የሚያዋርዱ ስቃዮች ደርሶባታል፣ በማንነቷ ላይ የተመሰረቱ ስድቦችን ተሰድባለች ፣ ሴትነቷን ተመስርተው ጥቃት እንደፈጸሙባት መናገሯ ይታወሳል። “ ሴት ሁኜ መፈጠሬን እንድትጠላ የሚያደርጉ ተግባራትን እንደተፈጸሙባት፣ እርቃኗን አቁመው እንደተሳለቁባት ፣ የእግር ጥፍሮቿን መርማሪዎቿ እንደነቀሉባት፣ ጥፍሮቿን ከነቀሉ በኋላም ጥፍሮቹ የነበሩበትን ቦታ ቁስል እየነካኩ እንዳሰቃዩዋት እንዲሁም ጸጉሯን በመንቀልም የኢ-ሰብዓዊ ተግባር ሰለባ

እንዳደረጉዋት ለፍርድ ቤት ባቀረበችው አቤቱታ አስታውቃ ነበር። ንግስት ከዚህ ሁሉ ስቃይ በሁዋላ በመጨረሻ ከእስር ቤት መውጣቷ ብዙዎች ደስታቸውን እየገለጹላት ነው። በተመሳሳይ ዜና በእነ ክንዱ ዱቤ የክስ መዝገብ 8ኛ ተከሳሽ ብርሃኑ አያሌው፣ 9ኛ ተከሳሽ መላኩ አለምን ጨምሮ አቶ መንገሻ ገ/ህይወት፣ ንጉሱ ድሪባ 9 ተከሳሾች ክሳቸው ተቋርጦ በነጻ ተፈትተዋል። አቶ ዘመነ ጌጤ፣ አቶ ለገሰ ወልደሃና አቶ ክንዱ ዱቤን ጨምሮ የሌሎች 8 ተከሳሾች ግን እስካሁን ክሳቸው አልተቋረጠም። በተጨማሪም በአርበኞች ግንቦት 7 ክስ የቀረበባቸው አቶ ኤርሚያስ ፀጋዬ፣ አቶ ፍሬው ተክሌ፣ አቶ ዳንኤል ተስፋዬና አቶ ቴዎድሮስ አስፋው አብረዋቸው የተከሰሱት በነጻ ቢሰናበቱም፣ እነሱ ግን አሁንም በእስር ላይ ይገኛሉ። በፌስቡክ ገጹ ላይ የገዥውን ህወሃት ኢህአዴግ አገዛዝ በማውገዝ ጽሁፍ በመጻፉ ብቻ ተፈርዶበት በእስር ላይ የሚገኘው የቀድሞው የሰማያዊ ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ የነበረው ወጣት ዮናታን ተስፋዬ “አጥፍቻለሁ ተፀፅቻለሁ” ብለህ ፈርም ተብሎ የቀረበለትን ፎርም አልፈርምም በማለቱ፣ አሁንም በእስር ላይ ይገኛል። ወጣት ዮናታን ወንጀል አልሰራሁም፣ አልፈርምም በሚለው አቋሙ አሁንም እንደጸና ነው። በምህረትና በይቅርታ የተወሰኑ እስረኞች እየተፈቱ ቢሆንም አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ፣ ወጣት ዮናታን ተስፋዬ፣ ዶ/ር ፍቅሩ ማሩን ጨምሮ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በተለያዩ እስር ቤቶች በስቃይ ላይ ይገኛሉ።

No comments:

Post a Comment