Wednesday, February 21, 2018

በጉራጌ ዞን የተጀመረው አድማ እንዲቆም ማድረጉን ዘርማ አስታወቀ።

 በዞኑ የሚካሄደውን ትግል የሚያስተባብረው የጉራጌ ወጣቶች ስብስብ ዘርማ ለአንድ ሳምንት ሲካሄድ የቆየውን የስራ ማቆም አድማ ዛሬ እንዲቆም ያደረገው ለቀጣዩ ትግል ተጠናክሮ ለመውጣት ነው ብሏል። በሁሉም የጉራጌ ወረዳዎች የሚደረግ አድማና ተቃውሞ ለማዘጋጀት በማቀድ ላይ መሆኑንም ለኢሳት በደረሰው መረጃ ላይ ተመልክቷል። ከዛሬ ጀምሮ ስራ ያቆሙ የንግድ ቦታዎችና ተሽከርካሪዎች ወደ እንቅስቃሴ እንዲገቡ ዘርማ መልዕክት አስተላልፍፏል። አድማውን መቆጣጠር ያልቻለው አገዛዙ፣ የአካባቢው ተወላጅ ባለስልጣናትንና የደህንነት ሃይሎችን በጋራ የያዘ ግብረሃይል ከአዲስ አበባ ወደ ወልቂጤ መላኩም ታውቋል። ዘርማ በጉራጊኛ ወጣት ማለት ነው። የጉራጌ ወጣቶች በዘርማ መጠሪያነት የጀመሩት ትግል እየተጠናከረ መምጣቱን መረጃዎች ያመለክታሉ። የካቲት 6 የጀመረው በቤት ውስጥ የመቀመጥ አድማ ዛሬ እንዲቆም መወሰኑን የገለጸው የጉራጌ ወጣቶች ስብስብ ዘርማ የጉራጌ ህዝብ ለተጠናከረ ትግል እንዲዘጋጅ ጥሪ አድርጓል። ወልቂጤ ሊገነባ የታቀደው የዘመናዊ ሆስፒታል ግንባታ ፕሮጀክት ወደትግራይ ተዛውሯል የሚል መረጃ ሰበብ ሆኖ የተጠራቀመ ብሶትና ምሬቱ ፈንቅሎ አድማ ያስጠራው የጉራጌው ተቃውሞ ለሳምንት ቆይቶ ዛሬ እንዲቆም ተወስኗል። የዛሬ ሳምንት ረቡዕ በወልቂጤ
ጀምሮ እንድብርና አገና ከተሞችን ያዳረሰው አድማ ወደ አደባባይ አመጽ ተቀይሮ የሶስት ሰዎች ህይወት መጥፋቱ የሚታወስ ነው። ኢሳት ያነጋገራቸው የዘርማ አስተባባሪዎች እንደሚሉት ህዝቡ መንግስትን መስማት በማቆሙ ሃላፊነት ያለው የትግል መልዕክት እየተቀበለ ያለው ከጉራጌ ወጣቶች ነው። ሰሞኑን የሀገር ሽማግሌዎችን ከየወረዳው በመሰብሰብ የህዝቡን አድማ ለማስቆም የተደረገው ጥረት አለመሳካቱ ታውቋል። ህዝቡ ከእንግዲህ እንዳትመጡብን ብሎ ሽማግሌዎቹን መመለሱን የጠቀሱት የኢሳት ምንጮች የዘርማዎች እንቅስቃሴ ተደራጅቶ ህዝቡ ጋ በመድረሱ ለአገዛዙ ከፍተኛ ስጋት መደቀኑም ተገልጿል። ዛሬ ለሳምንት የዘለቀው በቤት ውስጥ የመቀመጥና የስራ ማቆም አድማ ማብቃቱን ዘርማ ለኢሳት አስታውቋል። አስተባባሪዎቹ እንደሚሉት ለህዝቡ በተላለፈው መልዕክት መሰረት ዛሬ አድማው አብቅቶ እንቅስቃሴ ተጀምሯል። አድማውን በቁጥጥር ስር ማዋል ያልቻለው አገዛዙ ታዋቂ የሆኑ የጉራጌ ተወላጆችን፣ ባልስልጣናትንና የደህንነት ሃይሎችን የያዘ ግብረ ሃይል ከአዲስ አበባ ወደ ወልቂጤ መላኩ ተሰምቷል። መንግስትን መስማት አቁመናል ያሉ የወልቂጤ ነዋሪዎችን በመሰብሰብ ላይ መሆናቸውንም የደረሰን መረጃ አመልክቷል። ታዋቂ ሰዎችን ከፊት አስቀድመው ከኋላ ሆነው ስብሰባ ውስጥ የሚገኙት የአገዛዙ የደህንነት ሰዎች ከነዋሪው መሃል የተወሰኑትን ለማሰር እንደተዘጋጁም ታውቋል። ወጣቶችን አስቁሟቸው የሚል ተማጽኖ ለማቅረብ የመጣው ግብረሃይሉ ምንም ለውጥ አያመጣም ሲሉ የዘርማ አስተባባሪዎች ይናገራሉ። የህዝቡ ትግል ስርነቀል ለውጥ ለማምጣት በመሆኑ በልመናና በሃይል የሚቀለበስ አይሆንም ሲሉም ገልጸዋል። ዘርማ ለተቀናጀና በሁሉም የጉራጌ አካባቢዎች የሚካሄድ ጠንካራ አድማ ለማዘጋጀት በመምከር ላይ መሆኑንም አሰተባባሪዎቹ ይናገራሉ።

No comments:

Post a Comment