Tuesday, February 27, 2018

በነቀምት ውጥረቱ ተባብሶ መቀጠሉ ተገለጸ። ዛሬ ጠዋት አንድ ወጣት በአልሞ ተኳሽ ወታደር መገደሉን የደረሰን መረጃ አመልክቷል።

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጂን በመጣስ ተቃውሞ እያደረጉ ባሉ የነቀምት ነዋሪዎች ላይ ተኩስ የከፈቱት የአገዛዙ ወታደሮች ከ20 በላይ ሰዎች ማቁሰላቸውም ታውቋል። ቤት ለቤት አፈሳ የተጀመረ መሆኑኑም ተመልክቷል። የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ ኦፌኮ አመራሮች በወለጋ ደጋፊዎቻቸውን ለማግኘት ቀጠሮ የያዙት ከአስቸኳይ አዋጁ ይፋ መሆን ቀደም ብሎ ነበረ። አመራሮቹ መርሃ ግብራቸውን ጠብቀው በየከተሞቹ እየተገኙ ደጋፊዎቻቸውን ሲያነጋግሩ ቆይተው ወደ ነቀምት ያመራሉ። ነቀምት ለመድረስ 5 ኪሎ ሜትር ሲቀራቸው በኮማንድ ፖስቱ መታገታቸውን ነው መረጃዎች የሚያመለክቱት። የነቀምትን ስታዲየም ሞልቶ የሚጠብቃቸው ህዝብ ዜናውን ሲሰማ ወዲያኑ የተቃውሞ ድምጽ ማሰማት መጀመሩ በወቅቱ ተገልጿል። አስቸኳይ አዋጁ ስለሚከለክል ህዝብ መሰብሰብ አትችሉም የተባሉት የኦፌኮ አመራሮች ወደ አዲስ አበባ ሲመለሱ ነቀምት በተቃውሞ ተናወጠች። መንገዶች በተቃጠሉ ጎማዎች ተሞሉ። አገዛዙ ከስልጣን እንዲወርድ የሚጠይቁ መልዕክቶች አደባባይ በወጣው ህዝብ መስተጋባት ጀመሩ። ትላንት መሀል ነቀምት የጦርነት ቀጠና ይመስል ነበር። (ድምጽና
ቪዲዮ) ከመሪዎቻቸው ጋር እንዳይገናኙ የተደረጉት የነቀምቴ ነዋሪዎች በአስቸኳይ አዋጅ ውስጥ ሆነውም ተቃውሞአቸውን ቀጥለዋል። ዛሬም ህዝብ ጸረ መንግስት መልዕክቶችን ሲይሰማ እንደነበረ ታውቋል። በተለይ ዛሬ ጠዋት በዋና ዋና የነቀምት አውራ ጎዳናዎች ላይ ከፍተኛ የተቃውሞ እንቅስቃሴ እንድነበረ ተገልጿል። ከቀትር በኋላ ግን ከተማዋን የአገዛዙ ታጣቂዎች መውረራቸውን ከአከባቢው የመጣው ዜና ያስረዳል። የአንድ ወጣት ግድያን ተከትሎ ነቀምት ሙሉ በሙሉ በአገዛዙ ወታደሮች ቁጥጥር ስር መውደቋ ታውቋል። በመሃል ነቀምት አደባባይ ላይ በአልሞ ተኳሽ ጥይት የተገደለው ወጣት አበበ መኮንን የሚባል እንደሆነ ተገልጿል። ወጣት አበበ ከተገደለ በኋላ ለበርካታ ሰዓታት አስክሬኑ አደባባይ ላይ እንዲቆይ ተደርጓል። ከትላንት ጀምሮ በአገዛዙ ወታደሮች በተወሰደ እርምጃ ከ20 በላይ ሰዎች ቆስለው ሆስፒታል ገብተዋል። ከኦፌኮ አመራሮች የወለጋ ጉዞ ጋር በተያያዘ በተነሳ ተቃውሞ የሰው ህይወት ሲጠፋ የዛሬ ሁለተኛው ሲሆን ባለፈው ቅዳሜም በደምቢዶሎ አንድ ሰው መገደሉ ሲታወስ ፡ሰባት ቆስለዋል። መረጃዎች እንደሚያመለክቱት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን በመጣስ ተቃውሞውን በቀጠለው የነቀምት ነዋሪ ላይ ጥብቅ እርምጃ እንዲወሰድ በኮማንድ ፖስቱ ትዕዛዝ መሰጠቱን ተከትሎ በነቀምት ውጥረት ነግሷል። ለጊዜው ቁጥሩ ባይታወቅም በርካታ ሰዎች መታፈሳቸው ታውቋል። የከተማዋ እንቅስቃሴ የተቋረጠ ሲሆን በመንገዶች ላይ የሚታዩት የአገዛዙ ወታደሮች ብቻ መሆናቸውን በቪዲዮ ተደግፎ ከወጣው መረጃ ለማወቅ ተችሏል።

No comments:

Post a Comment