Friday, August 19, 2016

የአሜሪካ መንግስት ዜጎቹ በኢትዮጵያ ውስጥ በሚያደርጉት እንቅስቃሴ የጥንቃቄ እርምጃዎችን እንዲወስዱ አሳሰበ

ኢሳት (ነሃሴ 13 ፥ 20108)
በኦሮሚያና አማራ ክልሎች እየተካሄዱ ያሉ ህዝባዊ ተቃውሞዎች ወደ መዲናይቱ አዲስ አበባ ሊዛመቱ ይችላሉ በሚል የአሜሪካ መንግስት ዜጎች በእንቅስቃሴያቸው ላይ የጥንቃቄ እርምጃዎችን እንዲወስዱ አርብ አሳሰበ። 
በሃገሪቱ እየተካሄዱ ባሉ ተቃውሞዎች ዙሪያ መግለጫን ያወጣው የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በሁለቱ ክልሎች በመካሄድ ላይ ያለው ተቃውሞ ወደ ሌሎች ክልሎችና አዲስ አበባ ሊዛመት እንደሚችል ማሳሰቢያ መውጣቱን ሮይተርስ ዘግቧል። 
መቀመጫውን በአዲስ አበባ ያደረገው የሃገሪቱ ኢምባሲ በበኩሉ የኢንተርኔት አገግልሎቶችን ጨምሮ የሌሎች መገናኛ መንገዶች መስተጓጎል ከዜጎች ጋር በሚያደርገው ግንኙነት ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ አሳድሮበት እንደሚገኝ አስታውቋል።

በሃገሪቱ እየተካሄደ ያለውን ህዝባዊ ተቃውሞ ለመቆጣጠር ሲል መንግስት የማህበራዊ ድረገጾችን ጨምሮ የስልክና የተለያዩ የመገናኛ መንገዶችን በተደጋጋሚ ሲዘጋ መቆየቱ ይታወሳል።
በዚሁ የመንግስት እርምጃ ሰለባ መሆኑን ለመጀመሪያ ጊዜ ይፋ ያደረገው የኤሜሪካ ኤምባሲ በተለያዩ ጊዜያት ከዜጎቹ ጋር መረጃ ለመለዋወጥ የሚያደርገው ጥረት አድካሚ እንደሆነበት አስታውቋል።
በመካሄድ ላይ ያሉ ህዝባዊ ተቃውሞዎችን ለመቆጣጠር ሲል መንግስት የማህበራዊ ድረገጾችን ጨምሮ ሌሎች የመገኛኛ አገልግሎቶችን ሲዘጋ መቆየቱን የተለያዩ አካላት ሲገልጹ ቆይተዋል።
ከጥቂት ሳምንታት በፊት የአሜሪካ መንግስት በኦሮሚያ ክልል እየተስፋፋ የመጣውን ተቃውሞ ተከትሎ ዜጎች በክልሉ በሚያደርጉት የጉዞ እንቅስቃሴ ላይ የጥንቃቄ እርምጃን እንዲወስዱ ማሳሰቡ ይታወሳል።
መቀመጫቸውን በአዲስ አበባ ያደረጉ የተለያዩ ኤምባሲዎችና አለም አቀፍ ተቋማት ዜጎቻቸውና ሰራተኞቻቸው ተመሳሳይ ጥንቃቄን እንዲያደርጉ ማሳሰቢያዎችን እያሰራጩ እንደሚገኝ ከሃገር ቤት የተገኘው መረጃ አመልክቷል።

No comments:

Post a Comment