Wednesday, August 17, 2016

የአማራና ኦሮሞ ፊዴራል ፖሊስ አባላት ማስጠንቀቂያ ተሰጣቸው

ኢሳት (ነሃሴ 11 ፥ 2008)
የአማራና የኦሮሞ የፌደራል ፖሊስ አባላት ያልታጠቀ ህዝብ ላይ አንተኩስም ብለው አቋም መያዛቸውን ተከትሎ፣ የህወሃት ባለስልጣናት የአማራና የኦሮሞ የፌዴራል ፖሊስ አባላትን በምስጢር በመጥራት ዛቻና ማፈራሪያ መስጠታቸው ተነገረ። 
የህዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ ሃላፊዎች ሰሞኑን በአዲስ አበባ ከተማ ባደረጉት ስብሰባ ራሳችንን ለማዳን ምን ማድረግ አለብን በሚል የኦሮሞና የአማራ የፌዴራል ፖሊስ አባላትን በመለየት ማወያየታቸው ለኢሳት የደረሰው መረጃ ያስረዳል። 

“ከህወሃት ጋር ካልሆናችሁ የሚመጣው ሃይል ሊያጠፋችህ ነው” ያሉት የህወሃት ባለስልጣናት፣ የኦህዴድ አባላትንና ደጋፊያችሁን ኦነግ ከአገር ሊያስወጧችሁ ነው” ፣ የብዓዴን አባላትንና ደጋፊዎችን ደግሞ ግንቦት 7 ከአገር ሊያባርራችሁ ነው” በማለት የአብረን እንታገል ጥሪ ማቅረባቸውን ለኢሳት የደረሰው መረጃ አመልክቷል።
''ከእኛ ጋር ሆናችሁ በጋራ የመጣብንን አደጋ ካልመከትን እንደ ደርግ ወታደር ኮፊያ አንጥፋችሁ ትለምናላችሁ” ያሉት የህወሃት ባለስልጣን “የትግራይ ተወላጆች ወታደራችንን ይዘን ወደትግራይ እንገባለን፣ መብታችንንም እንጠቀማለን'' ሲሉ የህወሀቱ ፌደራል ፖሊስ ባለስልጣን ለአማራና ኦሮሞ ፌዴራል ፖሊስ አባላት መናገራቸው ተመልክቷል።
ስብሰባውን የመሩት የህወሃት የፌዴራል ፖሊስ ባለስልጣን ፊታቸው ላይ ተስፋ የመቁረጥ ሁኔታ ይታይባቸው እንደነበር የገለጹት የኢሳት ምንጮች፣ አሁን ለአማራና ለኦሮሞ ፌዴራል ፖሊስ አባላት የተሰጠው ማስጠንቀቂያ የምዕራብ አገራት ለህወሃት አመራር ጀርባ በመስጠታቸው እንደሆነም ታውቋል።
የህወሃት/ኢህአዴግ አመራር በኦሮሚያ እና በአማራ ክልሎች የፌዴራል ፖሊስና የጸጥታ ሃይል በማሰማራት ህዝባዊ ተቃውሞውን ለመጨፍለቅ ቢሞክርም፣ በአንዳንድ አካባቢዎች ፖሊሶች ከሰላማዊ ሰልፈኛው ጋር በመወገናቸው የህወሃትን አመራር በከፍተኛ ሁኔታ እንዳስደነገጠ ይነገራል።

No comments:

Post a Comment