Tuesday, July 15, 2014

ሰቆቃን ለማስቆም በጋራ እንነሳ!!! (የግንቦት 7)

ከወያኔ እስር ቤቶች የሚደርሱን መረጃዎች ህሊናን የሚረብሹ ናቸው። የትግራዩ ገዢ ጉጅሌ አባላት በእስር ላይ በሚገኙ ወገኖቻችን ላይ የሚፈጽሙት ሰቆቃ (ቶርቸር) በአስከፊ ሁኔታ ጨምሯል። በጭካኔው «ተወዳዳሪ የለውም» ሲባል በነበረው የደርግ ዘመን እንኳን የማይታወቁ የሰቆቃ ዓይነቶች ዛሬ በንፁሃን ዜጎች ላይ እየተፈጸሙ ነው።

ለማስረጃ ያህል:-
★ ወንዶች የዘር ፍሬዎቻቸውን በመዶሻ ይቀጠቀጣሉ፣
★ ሴቶች ጡቶቻቸውን ይረገጣሉ፤ ክብረ-ነክ ተግባራትም ይፈጸምባቸዋል፣
★ በኤሌክትሪክ በሚሰራ ማሞቂያ የእስረኞችን ጭንቅላት በማጋል እንዲሰቃዩ ይደረጋል፣
★ ከወንበር ጋር አቆራኝቶ ለሳምንት ያህል ማሰር በጣም እየተዘወተረ ያለ የሰቆቃ ዓይነት ሆኗል፣
★ በጠባብ ክፍል ውስጥ ለብቻ ዘግቶ ለወራት ማቆየት የተለመደ ነገር ነው፣
★ ከቆዳ በተሰራ ጅራፍ መግረፍ ድሮም ያለ ቢሆንም አሁን ተጠናክሮ ቀጥሏል፤ በደርግ ጊዜ የነበሩ ገራፊዎች ከያሉበት እየተፈለጉ እንደገና ለገረፋ ተቀጥረዋል፣
★ በሰብዓዊ ፍጡር ላይ ካራቴና ጁዶ መለማመድ፤ በስለት መቆራረጥ ወጣት የወያኔ «ተተኪዎች» የሚወዱት መዝናኛ ሆኗል፣

እነዚህና እነዚህን የመሳሰሉ አሰቃቂ የሰቆቃ ዓይነቶች የወያኔ እስር ቤቶች መለያ ባህሪያት ናቸው።

የትግራዩ ገዥ ጉጅሌ ሰላዮች ሰቆቃን የሚፈጽሙ ስለመሆኑ በገሃድ አምነው አያውቁም። ሆኖም ግን ሰቆቃን የሚፈጽሙት ተከልለውና ተደብቀው አይደለም። ስንቱ ነው ከተማ ውስጥ በሰው መሃል የተደበደበው? ስንቱ ነው በአደባባይ የተረገጠውና የተዋረደው? በጠራራ ፀሃይ፤ ከተማ ውስጥ፤ ህዝብ መሃል ይህንን የመሰለ ሰቆቃ የፈጸመን እስር ቤት ውስጥ ከዚህ አንድ ሺህ ጊዜ የከፋ ነገር ከመፈጸም ምን ያግደዋል?

በማናቸውም ምክንያት ሰቆቃ መፈጸም እጅግ የተወገዘ እና ምህረት የማያሰጥ ዓለም ዓቀፍ ወንጀል ነው። የደህንነት ስጋትም ሆነ አደጋ ለሰቆቃ በምክንያትነት ሊቀርብ አይችልም። ሰቆቃን ተቀባይነት ያለው የምርመራ ዘዴ የሚያደርግ የወንጀል ዓይነት የለም። «ወንጀል መከላከል» ለሰቆቃ ተቀባይነት የሌለው ምክንያታቸው ቢሆንም እንኳን ወያኔዎች እሱንም በምክንያትነት ማቅረብ አይችሉም። የወያኔ ሰላዮችና ፓሊሶች ሰቆቃን የሚፈጽሙት የሚመረምሩት ብርቱ ወንጀል ስላለ አይደለም። ወያኔዎች በወያኔ ዳኞች ጉዳያቸው ያለቀላቸውና ወያኔያዊ ፍርደገምድል ፍርድ የተሰጣቸው ፍርደኞችንም ጭምር ያሰቃያሉ። ለወያኔ የሰቆቃ እውነተኛ ምክንያቶች ሁለት ናቸው።

የመጀመሪያዉ እና ዋነኛው ምክንያታቸው የዘር ጥላቻ ነው። የወያኔ አረመኔዎች የአማራና የኦሮሞ ተወላጆች የሆኑ ግለሰቦችን በደበደቡና ባዋረዱ መጠን አማራንና ኦሮሞን ያዋረዱ ይመስላቸዋል። ለዘመናት በልባቸው ውስጥ የተጠራቀመውን ጥላቻ በግለሰቦች ላይ ይወጡታል። እነዚህ በክፋት የተሞሉ ሰዎች ሲገርፉና ሲደበድቡ የሚሳደቡት፣ የሚራገሙት የተደብዳቢውን ዘር እንጂ ተደብዳቢውን በግል አለመሆኑ የደረሰበት ሁሉ ያውቀዋል።

ሁለተኛው ምክንያት የጉጅሌው አባላትና ተባባሪዎች ሰውን በማሰቃየት የሚደሰቱ እኩያን መሆናቸው ነው። ይህ የስነልቡና ህመም ምንጩ በራስ የመተማመን እጦት ነው። መንፈሰ ደካማ ሰው ውስጡ እየነገረው ያለውን ደካማነት በእጆቹ በሚሰነዝረው ዱላ ማስተባበል ይፈልጋል። የትግራይ ገዢ ጉጅሌ እና ተባባሪዎቹ የሚያደርጉት ይህንኑ ነው። እጃቸው ውስጥ የገቡትን ወገኖቻችንን በማሰቃየት ትንሽነታቸውን ማሸነፍ ይፈልጋሉ።

ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ በወገኖቻችን ላይ ዘግናኝ ሰቆቃዎችን በማድረስ ላይ ለምትገኙ የትግራይ ገዥ ጉጅሌ አባላት፣ ለቅጥረኞቻቸውና ተባባሪዎቻቸው በሙሉ ጥብቅ ማስጠንቀቂያ ይሰጣል። ሰቆቃ ፈጽሞ ማምለጥ እንደማይቻል በደርግ ጊዜ የሰቆቃ ቀንደኛ መሪ ከነበረውና በአሜሪካ አገር ተከሶ ዛሬ በናንተው እስር ቤት ከሚገኘው ቀልቤሳ ነጌዎ ትምህርት ውሰዱ። የእናንተም መጨረሻ ከእነሱ የባሰ እንጂ የተሻለ እንደማይሆን ተገንዘቡ።

ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!


No comments:

Post a Comment