Thursday, April 12, 2018

የአዲስአበባና የድሬደዋ ምርጫ በአንድ አመት እንዲራዘም ተወሰነ

(ኢሳት ዲሲ–ሚያዚያ 4/2010)በዚህ አመት መካሄድ የነበረበት የአዲስአበባና የድሬደዋ ምርጫ እንዲሁም በመላ ሃገሪቱ የሚካሄዱ የአካባቢና ማሟያ ምርጫ በአንድ አመት እንዲራዘሙ ፓርላማው ዛሬ ወሰነ።
ከአመት በኋላም ምርጫው መቼ ይካሄዳል ለሚለው ወርና ቀን ተቆርጦ አልተቀመጠለትም። 8 የፓርላማ አባላትም ድምጸ ተአቅቦ ማድረጋቸው ተሰምቷል።
ከ230 በላይ የፓርላማ አባላትም አልተገኙም። የሕወሃቱ ኤፈርት ንብረት የሆነው ሬዲዮ ፋና እንደዘገበው በፓርላማው የዛሬ ውሎ የማሟያ ምርጫም ለአንድ አመት ተራዝሟል።
ፓርላማው ዛሬ ሚያዚያ 4/2010 ባካሄደው መደበኛ ስብሰባ የአዲስ አበባና የድሬደዋ ምክር ቤቶች በየአምስት አመት የሚያካሂዱት ምርጫም ወደሚቀጥለው አመት ተሻግሯል።
የአዲስ አበባ ምርጫ በዚህ በሚያዚያ ወር መካሄድ የሚጠበቅበት ሲሆን በምርጫው ከተማዋን የሚያስተዳድሩ ሃላፊዎች ከንቲባው ጭምር የሚመረጡበት እንደሆነም ታውቋል።

ይህም ለአንድ አመት ተራዝሟል። ከአዲስ አበባና ድሬደዋ የከተማ ምክር ቤት ምርጫ በተጨማሪ በመላ ሀገሪቱ የሚካሄዱ የአካባቢና የማሟያ ምርጫዎችም በተመሳሳይ ለአንድ አመት እንዲራዘሙ ተወስኗል።
የተራዘሙት ምርጫዎች በ2011 እንደሚካሄዱ ቢገለጽም ከአመት በኋላ ምርጫዎቹ በየትኛው ወር እንደሚካሄዱ ግን በግልጽ አልተቀመጠም ።
ወሩ መቼ ነው በሚልም ከፓርላማ አባላት ለቀረበው ጥያቄ አሁን መወሰን አይቻልም የሚል ምላሽ ከምክትል አፈጉባኤው ተሰቷል።
ምክትል አፈጉባኤዋ ወይዘሮ ሽታዬ ማናለ እንደገለጹት በጉዳዩ ላይ የብዙ አካላት ምክክር ስለሚያስፈልግ ቀኑን መወሰን አልተቻለም።
በመጨረሻም በ8 ተአቅቦ ውሳኔው መጽደቁ ይፋ ሆኗል። ሆኖም ከ547 የምክር ቤት አባላት የተገኙት 310 ብቻ ናቸው።
ከ230 በላይ የምክር ቤት አባላት በስብሰባው ላይ አልተገኙም። የሕወሃት ንብረት የሆነው ሬዲዮ ፋና እንደዘገበው የማሟያ ምርጫም በአንድ አመት እንዲራዘም ተወስኗል።
ይህም የትግራይ ክልል ምክር ቤት አባል ሳይሆኑ የትግራይ ክልልን በምክትል ፕሬዝዳንትነት የሚመሩት ዶክተር ደብረጺዮን ገብረሚካኤል ለተጨማሪ አመት ያለውክልና በስልጣን ላይ ይቆያሉ ማለት ነው።

No comments:

Post a Comment