Wednesday, April 18, 2018

በወልዲያ እግር ኳስ ቡድን ላይ የተጣለውን ቅጣት በመቃወም በአዲስ አበባ ከተማ የቡድኑ ደጋፊዎችና አጋሮቻቸው ተቃውሟቸውን አሰሙ፤ አሰልጣኝ ስዩም አባተ ታመው ሆስፒታል ገቡ

 (ኢሳት ዜና ሚያዝያ 10 ቀን 2010 ዓ/ም) በመላው ኢትዮጵይያ በእግር ኳስ ሜዳዎች ከከስፖርት መርህ ውጪ ስርዓት አልበኝነት ከጊዜ ወደጊዜ እየተሳፋ መጥቷል። በዚህም የብዙ ሰላማዊ ዜጎች ህይወትና ንብረት ለመውደም ምክንያት ሆኗል። ችግሩን ከመሰርቱ እንዲፈታ ወቅታዊ የሕግ እርምጃዎች መውሰድ የነበረበት የእግርኳስ ማኅበሩ ስርዓት አልበኝነትን ወደጎን በማለት ለችግሩ መባባስ ቀዳሚው ተጠያቂ ነው። ሰሞኑን ወልዲያ ላይ በሼክ መሀመድ ሁሴን አላሙዲን መጫወቻ ሜዳ በወልዲያና በፋሲል ከነማ መሃከል ተደርጎ በነበረው ጫወታ ላይ አወዛጋቢ የሆነውን የዳኛውን ውሳኔ በመቃወም በደጋፊዎች መሃከል ረብሻ ተፈጥሮ በደጋፊዎችና በንብረት ላይ ጉዳት ደርስዋል። ይህን ተከትሎ የኢትዮጵያ እግር ኳስ የዲሲፕሊን ኮሚቴ ስምንት ነጥብ ያለው የቅጣት ብያኔ አሳልፍዋል። ለፋሲል ከተማ ፎርፌ እንዲሰጥ። ይህም 3 ነጥብ እና 3 ጎል እንዲሰጠው፣ የሚጫወትበት የመሀመድ ሁሴን አላሙዲን ስታድየም ለአንድ ዓመት ጨዋታ እንዳይካሄድ። ቀሪ የሜዳው ጨዋታዎችን ከወልዲያ በ500 ኪ.ሜ ርቀት እንዲያደርግ። 250 ሺህ ብር ቅጣት። የዳኞች ህክምና ወጪ እንዲሸፍን። አሰልጣኝ ዘማርያም ወልደጊዮርጊስ የአንድ ዓመት እገዳ እና 10 ሽህ ብር፣ ብሩክ ቃልቦሬ የአንድ ዓመት እገዳ እና 10 ሽህብር ቅጣት እንዲቀጡ የኢትዮጵያ እግር ኳስ የዲሲፕሊን ኮሚቴ ወስኗል። የኢትዮጵያ እግር ኳስ ማኅበር ቀድም ብሎ ሃዋሳ ላይ በኢትዮጵያ ቡና ደጋፊ ላይ እስከ ግድያ የደረሰ
ኢሰብዓዊ እርምጃ ሲወሰድ ዝም ማለቱ፣ ጎንደር ላይ በፋሲል ከነማና በኢትዮጵያ ቡን ደጋፊዎች መሃከል ተፈጥሮ የነበረውን ስርዓት አልበኝነት ቸል ማለቱ፣ በወልዋሎ እና መቀሌ ከተማ መሃከል የተፈጠረውን ረብሻ ካለቅጣት ማለፉን ተክትሎ በወልዲያ ከነማ ላይ በተናጠል የተወሰነው የቅጣት ውሳኔ አግባብነትን የተከተለ አይደለም ተብሎለታል። በሌሎች የእግር ኳስ ቡድኖች መሃከል የተከሰቱ ስርዓት አልበኝነትን ሳያወግዙ የወልዲያውን ብቻ እንዲራገብ ያደረጉት የገዥው ፓርቲ ልሳናትና የግል መገናኛ ብዙሃን ከውሳኔው ጀርባ ፖለቲካዊ አደምታ ሳይኖረው አይቀርም የሚለውን እንደማጠናከሪያ ተደርጎ ተወስዷል። በዛሬው እለት ወልዲያ ከተማ ከመቀሌ ከተማ በሚያደርጉት ጫወታ ላይ የቡድኑ ደጋፊዎችና አጋሮቻቸው የእግር ኳስ ማኅበሩን ውሳኔ፣ የመገናኛ ብዙሃን ሚዛናዊነት የጎደለው ዘገባ በማውገዝ ”ፍትሕ ለወልዲያ” የሚል መፈክር አንግበው ተቃውሟቸውን አሰምተዋል። አድሏዊውን ውሳኔ በዝማሬና በራሪ ወረቀቶች በመበተን በኢትዮጵያ ቴሌቪዥንና በእግር ኳስ ማህበሩን ዋና ጽ/ቤት ደጃፍ ላይ ውሳኔውን ዳግም እንዲታይ ጠይቀዋል። ጫወታው 1-1 በሆነ አቻ ውጤት ተጠናቋል። በኢትዮጵያ እግር ኳስ ውስጥ ከተጫዋችነት እስከ አሰልጣኝነት ስምና ዝናን ካተረፉ የአገሪቱ የመስኩ ባለውለተኛ ባሙያዎች አንዱ የሆኑት አሰልጣኝ ስዩም አባተ ታመው ዳግም ሆስፒታል ገብተዋል። አሰልጣኙ የተሻለ ሕክምናቸውን በውጭ አገራት እንዲያገኙ ቤሰቦቻቸው መጠየቃቸው ይታወሳል።

No comments:

Post a Comment