Wednesday, November 26, 2014

ቆንጆ መጽሔት ተከሰሰች

ከሁለት ሳምንት በፊት ከማዕከላዊ የምርመራ ቢሮ ከወዲያኛው ጫፍ የደወለው ሰው እንደነገረኝ ‹‹ከፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ነው›› ብሎ ደወለልኝ፡፡ ደዋዩ ቆንጆ መጽሔት መሆኑን ካጣራ በኋላ ዋና አዘጋጇ ስልክ ላይ ብደውል ዝግ ነው ፤ ጥር ወር ላይ ባወጣችሁት ዘገባ እኛ ጋ ክስ ተመስርቶባችኋል አለኝ፡፡ ስለሆነም ለዋና አዘጋጇ መልዕክት አድርሱ መጥታ ቃሏን ትስጥ አለኝ፡፡ ለጊዜው በቅርብ እንደሌለች ነገርኩት፡፡ ‹‹እሺ›› ብሎ ስልኩን ዘጋው፡፡ ድጋሚ ባለፈው ሳምንት አንድ ስልክ ተደወለ፡፡ በወቅቱ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ስለነበርኩ ስልኩን ማንሳት አልቻልኩም፡፡ ስወጣ ግን ደወልኩ፡፡ ስልኩን ያነሳችው ሴት ‹‹የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ዋና (ማዞሪያ ስልክ)›› መሆኑን ነገረችኝ፡፡ እንግዲህ ይህ ስልክ ግቢ ውስጥ ያሉት አብዛኞቹ የሚጠቀሙበት በመሆኑ እንደ እኔ ሞባይሉ ላይ ሚስድ ኮል አይቶ መልሶ ለደወለ ማን እንደደወለለት ገና ተጠያይቆ ነው የሚታወቀው፡፡

ትናንት የደወለችው ግን ቁጣ በተቀላቀለው ንግግር ‹‹ለምንድነው ስልክ የማታነሱት›› አለች፡፡ ጋዜጣዊ መግለጫ፤ ኢንተርቪውና ሌሎች ጥሞና የሚፈልጉ (የስልክ ድምጽ የሚረብሹ) ስራዎች ላይ ለሆነ ጋዜጠኛ ስክል ያለማንሳት የተለመደ ጉዳይ መሆኑን ላስረዳት ሞከርኩ፡፡ ስንትን በስንት እንዳባዛችው ባይታወቅም በተደጋጋሚ ጊዜ መደወሏን ተናግራ ‹‹ለረቡዕ ጠዋት ማዕከላዊ መጥተው ቃሎትን እንዲሰጡ›› አለች፡፡
በዚህ ጉዳይ ጥር ላይ ያሳተማችሁት ዕትም ስለተባልኩ ባለፈው ዓመት ጥር ወር ላይ ያሳተምናቸውን ሁለት ዕትሞች ደግሜ ለማየት ሞከርኩ፡፡ የታየኝ ነገር የለም፡፡ እንግዲህ እነሱ የታያቸው ነገር ይኖራል፡፡ በዚያ ላይ ከሳሽ ማን እንደሆነ አልታወቀም፡፡ አቃቤ ህግ? መንግስት? ግለሰብ? ማህበር?. . . የታወቀ ነገር የለም፡፡
ባለፈው ዓመት የዛሬው ኢቢሲ የአምናው ኢቲቪ በሰራው ተከታታይ የዶክመንተሪ ፊልም ምክኒያት በብዙ መጽሔቶችና ጋዜጦች ላይ ክስ ተመስርቶ የቆንጆ መጽሔት አዘጋጆችን ጨምሮ በርካታ ጋዜጠኞች ለስደት ተዳርገዋል፡፡ ተመስገን ደሳለኝንና ብዙ ጋዜጠኞች ለእስር ተዳርገዋል፡፡ ዶክመንተሪው የግል የህትመት ውጤቶችን በሙሉ ሀጢአተኛ አድርጎ ስለፈረጀ ማተሚያ ቤቶች ጋዜጣና መጽሔቶችን ማተም ፈርተዋል፡፡ ዶክመንተሪው የግል ሚዲያውን ብቻ ሳይሆን ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎችን የግንቦት 7 እና የሻዕቢያ ተላላኪ፤ የታሰሩ ሙስሊሞችን ገና ጉዳያቸው በፍ/ቤት እየታየ ባለበት ሁኔታ ላይ አክራሪ፤ ብሎገርና ሌሎችንም ስም እየሰጡና እየፈረጁ በፍ/ቤቶች ላይ ጫና እስከማሳደር የሚደርስ ዘገባዎች ሲሰራጩ ኢቲቪ ነውና ማንም አይጠይቀውም፡፡ የግሉ ሚዲያ ላይ ሲሆን ግን. . .
አዲስ አድማስ ጋዜጣ ባለፈው ቅዳሜ ለንባብ እንዳበቃው የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለስልጣን ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባቀረበው ሪፖርት ላይ አሁንም ክስ የሚመሰረትባቸው የህትመት ውጤቶች መኖራቸውን ጠቁሟል፡፡ በዚህ መልኩ ወደ ፊት በኢትዮጵያ ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ ውጪ የህትመት ውጤቶች ስለመኖራቸው እንድንጠራጠር ያደርገናል፡፡
ጋዜጠኞችን በማሰርና በማሳደድ የቀዳሚነቱን ስፍራ የተቆናጠጠችው ሀገራችን የወደፊት የዴሞክራሲ እጣ ፈንታዋ ምን ይሆን? ይህ ነገር በዚሁ እንዳይቀጥል፤ የጋዜጠኞች እስርና ስደት እንዲቆም ከመንግስት ኃላፊዎች ጋር ቀርቦ ለመነጋገር የተደረገው ጥረት በኃላፊዎቹ ግትርነት መፍትሔ ማግኘት አልቻለም፡፡ ‹‹የተሰደደና የታሰረ ጋዜጠኛ የለም›› እስከማለት ደርሰዋል አይናቸውን በጨው አጥበው፡፡ የጋዜጠኞች እስርና ስደት የሀገርንና የመንግስትን ስም ጥቁር ጥላሸት ከመቀባት ውጪ ለሀገርም ለህዝብም የሚጠቅም ነገር ያለመኖሩን በተደጋጋሚ ቢነገርም ሹማምንቱ ጆሮ ዳባ ልበስ ብለዋል፡፡
የነገው የማዕከላዊ ቀጠሮዬን እያሰብኩ ይህቺን ሰነቅኩላችሁ፡፡


No comments:

Post a Comment