Friday, July 7, 2017

የኢትዮጵያ ፓርላማ ከ320 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት አጸደቀ

(ኢሳት ዜና - ሰኔ 30 2009) 
የኢትዮጵያ ፓርላማ የቀረበለትን ከ320 ቢሊዮን ብር በላይ አመታዊ በጀት አጸደቀ ።
ይህ በጀር ካለፈው አመት ጋር ሲነጻጸርበ17 በመቶ ብልጫ ያለው ቢሆንም የበጀት ጉድለቱ ግን የአጠቃላይ መጠኑ 1/3ኛ መሆኑን ለምወቅ ተችሏል ። ከካፒታል በጀት ከ1114 ቢሊዮን ብር በላይ ሲመደብ ለአጠቃላይ የወጪ በጀት ደግሞ 81.8 ቢሊዮን ብር ተመድቧል ።የ100 ቢሊዮን ብር የበጀት ጉድለት ያለበት የመንግስት አመታዊ በጀት ከብድር እና እርዳታ ይገኛል ጠብሎ እንደሚጠበቅ ተገልጿል ።ዋናው ገቢ ግን ከግብርና ከሃገር ውስጥ የሚሰበሰብ ነው ተብሏል ።በበጀት እቅዱ ላይ የቀረበው መረጃ እንደሚያመለክተው ለልማት የሚውለው ገንዘብ ሲቀንስ ለመከላከያና ለጦር መሳሪያ የሚወጣው ግን ጨምሯል ።በዚሁም መሰረት የመከላከያ በጀቱ አምና 11 ቢሊዮን ብር እንዲሆን ተደርጓል ።የልማት ፕሮጀክት በጀቱ ደግሞ አምና 12 ቢሊዮን የነበረው ዘንድሮ ወደ 7 ቢሊዮን ብር እንዲወርድ ተደርጓል ተብሏል ። ኢትዮጵያ ያለባት የብድር ጫና ከ5 መቶ ቢሊዮን ብር በላይ መድረሱና ካለፈው አመት ጋር ሲነጻጸር በ35 ቢሊዮን ብር መጨመሩ መገለጹ ይታወሳል ። ከውጭ ንግድ ገቢ ኢትዮጵያ የምታገኘው ገቢ ደግሞ ካለፈው አመት ጋር ሲነጻጸር በ5 ቢሊዮን ቀንሷል ። ከፍተኛ የገንዘብ ግሽበት ባለባት ኢትዮጵያ የእዳ ጫናውና የውጪ ምንዛሪ እጥረት በሃገሪቱ የኢኮኖሚ ሁኔታ ላይ ችግር እየፈጠረ መሆኑን ባለሙያዎች ይናገራሉ ። 

ይህ በእንዲህ እንዳለም የትግራይ ክልል ምክር ቤት ከ12 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት ማጽደቁ ተነግሯል ። የኢትዮጵያ በጀት ከ320 ቢሊዮን ብር በላይ ሆኖ ቢጸድቅም የበጀት ጉድለቱ ከ100 ቢሊዮን ብር በላይ መሆኑ ብድር ወይም እርዳታ ባይገኝ እንዴት ይሸፈናል የሚለው ግልጽ አይደለም ። ከዚህ ቀደም በነበረው አሰራር መንግስት ከብሄራዊ ባንክ ሲበደር መቆየቱ ቢታወቅም ይህ አመራር በኢኮኖሚው ላይ ችግር በማስከተሉ እንዲቀር መደረጉ ይነገራል ።
(ኢሳት ዜና – ሰኔ 30 2009) ደቡብ ምስራቅ ኢትዮጵያና ሶማሊያን ጨምሮ በአፍሪካ ቀንድ የሚያስፈልገው አስቸኳይ የምግብ ዋስትና እርዳታ ለቀጣዩም የ2018 አመት ካልቀረበ ከፍተኛ አደጋና ችግር ሊያስከትል እንደሚችል አንድ አለም አቀፍ ተቋም አስጠነቀቀ ። የረሃብ አደጋን ቀድሞ በማስጠንቀቅ የሚታወቀውና ፊውስኔት የተባለው አለም አቀፍ ተቋም እንዳስጠነቀቀው የዘንድሮው አመት የዝናብ መጠን አጥጋቢ ባለመሆኑ አስቸኳይ የምግብ እርዳታው ለአፍሪካ ቀንድ ሃገራት በሚቀጥለው አመትም ካልቀረበ አደጋው የከፋ ሊሆን ይችላል ።በተለይም በደቡብ ምስራቅ ኢትዮጵያና በሶማሊያ እጅግ የከፋ የምግብ እጥረት ሊከሰት እንደሚችል ተቋሙ አስጠንቅቋል ። በአለም አቀፍ ተቋሙ መግለጫ መሰረት ከነዚሁ ሃገሮች በተጨማሪም በኬንያ ፣በየመን ፣ በደቡብ ሱዳንና በሌሎችም የአፍሪካ ቀንድ ሃገራት ችግሩ ተባብሶ ሊቀጥል ይችላል ።እንደ ፊውስኔት መግለጫ በአፍሪካ ቀንድ በተለይም በአርብቶ አደር አካባቢዎች የሚላስና የሚቀመስ ምግብ በቀጣዩ የፈረንጆች አመት ማለትም በ2018 ላይም ላይኖር ይችላል ። እናም አስቸኳይ የምግብ ዋስትና እርዳታው ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ተቋሙ ጥሪ አቅርቧል ። በተለይ ደግሞ በኢትዮጵያ ቆሬ ዞን እንዲሁም ሙዳግ እና ጋላግዱድ በተባሉ የሶማሊያ ዞኖች የዝናቡ መጠን ከ50 በመቶ በታች ዝቅ በማለቱ ችግሩ የከፋ ሊሆን እንደሚችል ተተንብዩል ። በኢትዮጵያ ሶማሊ ክልል በዋርዴርና ቆሬ ዞኖች ካለፉት 36 አመታት ወዲህ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ የዝናብ መጠኑ አነስተኛ በመሆኑ የከፋ ድርቅ እና ረሃብ ሊከሰት እንደሚችል ተገምቷል ። በኢትዮጵያ በአሁኑ ጊዜ ከ7.7 ሚሊዮን ህዝብ በላይ በከፋ የምግብ እጥረት ውስጥ የሚገኝ በመሆኑ አለም አቀፍ የረድኤት ድርጅቶች እርዳታ እንዲሰጡ ጥር እየቀረበላቸው ይገኛል ።በሃገሪቱ የሚገኘው አገዛዝ ግን አለም አቀፍ እርዳታውን ቢፈልገውም ያለምንም እገዛ ድርቁን መቋቋም እችላለሁ በማለት ተደጋጋሚ መግለጫ ሲሰጥ መቆየቱ ይታወሳል ። ይህም ሆኖ ግን በድርቁ ሳቢያ በተለይም በሶማሌ ክልል በርካታ ህጻናት መሞታቸውን የአለም የምግብ ድርጅትን ጨምሮ አለም አቀፍ የረድኤት ድርጅቶች ሲገልጹ መቆየታቸው አይዘነጋም ።

No comments:

Post a Comment