Monday, June 8, 2015

አቃቢ ህግ በእስር ላይ በሚገኙ ታዋቂ ፖለቲከኞች ላይ ምስክሮችን ማሰማት ጀመረ

ሰኔ ፩(አንድ) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በእነ ዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ በተከሰሱት በአብርሃ ደስታ፣ የሺዋስ አሰፋ፣ ሀብታሙ አያሌው፣ ዳንኤል ሺበሽና ሌሎች ስድስት ተከሳሾች ላይ አቃቤ ህግ በከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ አቅርቦ ማሰማት ጀምሯል።


አቃቢ ህግ “ምስክሮቼ ዛቻና ማስፈራሪያ ደርሶባቸዋል” በሚል ችሎቱ ምስክሮችን በዝግ እንዲያሰማ እንዲፈቅድለት ጠይቋል። ተከሳሾች በበኩላቸው የአቃቢ ህጉን መከራከሪያ አጥብቀው መቃወማቸውን ነገረ ኢትዮጵያ ዘግቧል።
የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ ምክትል የድርጅት ጉዳይ ሃላፊ እና ደቡብ ክልል ተወካይ አቶ ዳንኤል ሽበሺ ‹‹አቃቤ ህግ እስከ ሞት በሚያደርስ ወንጀል ከሶናል፤ ይህን ጉዳይ በግልጽ መከታተል አለብን፡፡ እናንተ ብቻ ሳትሆኑ የኢትዮጵያ ህዝብም መፍረድ አለበት›› በማለት ችሎቱ ምስክሮችን በግልጽ እንዲሰማ ጠይቋል። ሌላው የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ የነበረው አቶ ሀብታሙ አያሌው በበኩሉ ‹‹እኛ ዋስትና ተከልክለን በእስር ቤት ነን፤ የምስክሮች ስም ዝርዝር እንኳ አልተገለጸልንም፡፡ ታዲያ ማን ነው ምስክሮች ላይ ዛቻና ማስፈራሪያ የሚያደርስባቸው?›› ሲል አቃቤ ህግ ያቀረበው ምክንያት ተቀባይነት እንደሌለው አስረድቷል።


አቶ ሀብታሙ ሁሉንም ተከሳሾች በመወከል “በዝግ ችሎት ምስክሮችን የምትሰሙ ከሆነ ዛሬውኑ የግፍ ፍርደኞች ሆነን ወደ እስር ቤት ለመመለስ ዝግጁዎች ነን፤ ከዚህ በኋላም አንዳችንም ክርክር አናደርግም፡፡›› ብሎአል።ፍርድ ቤቱ በመጨረሻ የአቃቤ ህግ ምስክሮች በግልጽ ችሎት እንዲሰሙ ቢወስንም፣ የህትመትም ሆነ የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያዎች የምስክሮችን ቃል ዝርዝር በተመለከተ መዘገብ አይችሉም ሲል ውሳኔ አስተላልፎአል።አምስተኛ ተከሳሽ የሆነው የሰማያዊ ፓርቲ አመራር አቶ የሺዋስ አሰፋ ዳኞቹ ሲሰየሙና ስሙ ሲጠራ ከመቀመጫው ባለመነሳት በችሎቱ ላይ ተቃውሞውን መግለጹን ጋዜጣው ዘግቧል፡፡ አቶ የሺዋስ ዳኞቹ ለምን እንደማይነሳ ሲጠይቁት በዝምታ ያለፋቸው ሲሆን፣ ተነስ ሲባልም ያለምንም ንግግር በተቀመጠበት ተረጋግቶ በመቀመጥ ሳይነሳ ቀርቷል።

ከእስር ቤት ዜና ሳንወጣ ” ያለምንም ደም ኢህአዴግ ይውደም” ብለው የተናገሩ ወጣቶች በቂርቆስ ምድብ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ክስ ተመሰረተባቸው። ጌታሁን ታምራት፣ ዮሃንስ ስንታየሁ፣ ዮናስ በየነ ፣ አክሊሉ ወንድማገኝ እንዲሁም ብሩክ አሰፋ የተባሉት በ19 እና 22 አመት የእድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ወጣቶች ፣ በ17/ 09/07 ዓም በግምት ከምሽቱ 3 ፡30 ሰአት ሲሆን በምርጫ ማግስት በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ቀበሌ 04 ክልል ልዩ ቦታው መስቀል ፍላወር ወደ ቦሌ በሚወስደው አዲሱ የህዝብ መተላላፊያ በሆነ መንገድ ላይ እየተንቀሳቀሱ ፣ ጌታሁን ታምራትና ዮሃንስ ስንታየሁ ‘ያለምንም ደም ኢህአዴግ ይውደም፣ ሰማያዊ ፓርቲ የእኛ’ ሲሉ፣ ዮሃንስ በየነ አክሊሉ ወንድማገኝ እና ብሩክ አሰፋ ደግሞ ይህንኑ ንግግር በድጋሜ በማሰማት በዜማ ጮክ ብለው ደጋግመው እየተቀባባሉ በማሰማት ሌሎችን ህገወጥ ለሆነ ተግባር እንዲነሳሱ በንግግር በማሰማታቸው ፣ የማነሳሳት ጠባይ ያላቸውን የሃሳብ መግለጫዎች በማሰማት ወንጀል መከሰሳቸውን የክስ ሰነዱ ያሳያል።


No comments:

Post a Comment