Saturday, June 13, 2015

የፌደራል ጸረ ሙስና ኮሚሽን የባለስልጣኖችን ሃብት ይፋ ለማድረግ ወኔው አንሶታል ተባለ

ሰኔ ፭ (አምስት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የፌዴራል የሥነምግባርና የጸረ ሙስና ኮምሽን የመንግስት ተሿሚዎችን፣ ተመራጮችንና የመንግስት ሠራተኞች ሃብት የመመዝገብ ሥራዎችን ከ2003 ዓ.ም ጀምሮ እያከናወነ ቢሆንም ባሉበት
ጫናዎች ምክንያት መረጃውን ለሕዝብ ይፋ ለማድረግ አለመቻሉን ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ምንጮች ጠቆሙ፡፡
ኮምሽኑ የባለስልጣናትን ሀብት እንዲመዘግብ ስልጣን ሲሰጠው በመንግስትና በሕዝብ መካከል መተማመን ይፈጥራል ተብሎ ነው፣ ይሁን እንጅ ኮምሽኑ የባለስልጣናቱን ሃብት ምዝገባ ከማካሄድ በስተቀር ለመገናኛ ብዙሃንና ለሕዝብ ይፋ
ለማድረግ ድፍረቱን አላገኘም፡፡
የሐብት ማሳወቅና ምዝገባ መረጃዎች በቀላሉ ለተጠቂዎች ተደራሽ ለማድረግ የሐብት አስመዝጋቢዎችን የምዝገባ መረጃ በአግባቡ ለይቶና የሰነድ መለያ ኮድ ተሰጥቶት ተደራሽ በሚሆንበት አግባብ መደራጀቱን ኮምሽኑ ለሕዝብ ይፋ ካደረገ ከአንድ ዓመት በላይ የሆነው ቢሆንም፣ አሁንም ይህንን የምዝገባ መረጃ ይፋ ለማድረግ ባለበት ጫና ምክንያት ማድረግ ሳይችል ቀርቷል።

ኮምሽኑ ምዝገባውን ካጠናቀቀ በሃላ የምዝገባውን መረጃ ለሕዝብ ይፋ ሲያደርግ በምዝገባ ወቅት ሐብቱን በትክክል የላስመዘገበ፣ ያሸሸ ወይንም የደበቀ ባለስልጣን ወይንም ሹም ካለ ከሕዝብ በሚቀርብ ጥቆማና መረጃ ግለሰቡን ለመጠየቅ አቅዶ
የነበረ ቢሆንም ይህን ሥራ ደፍሮ የሚያስፈጽም በመጥፋቱ ምክንያት ሳይከናወን መቅረቱ ምንጫችን ጠቁሟል፡፡
የኢህአዴግ ከፍተኛ በለስልጣናትና ከፍተኛ የፓርቲ መሪዎች ከገቢያቸው በላይ የሚኖሩ መሆናቸው የሚታወቅ ሲሆን ከፓርቲው ጋር በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ንክኪ ያላቸው ሹማምንትም ኑሮአቸውና ገቢቸው ጨርሶ የማይገኛኝ መሆኑ
በየጊዜው ትችት ይቀርብበታል።
አንድ ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው የኮምሽኑ ሠራተኛ በአንድ መድረክ ላይ ” አንድ ሹም ከገቢው በላይ እየኖረ መሆኑን ለማረጋገጥ ግፋ ቢል በወር ከ5 ሺ ብር በላይ የማይበልጥ ደመወዙን እያሰቡ በአንጻሩ ግን ልጆቹን የሚስተምርባቸው
ውድ ት/ቤቶች፣ ባለቤቱና ዘመዶቹ የሚይዙዋቸው ውድ መኪናዎች፣ የሚዝናናባቸው ቦታዎች እንዲሁም የግሉን መኖሪያ ቤትና የገነባውን ሕንጻ፣ በሚስቱና በዘመዶቹ ስም የሚያካሂደውን ቢዝነስ ወዘ በማጥናት ብቻ ከገቢው በላይ እየኖረ
መሆኑን በቀላሉ መለየት እንደሚቻል” ተናግረዋል። በዚህ ዓይነት ሙስና ውስጥ የተዘፈቁ በርካታ ሹማምንት በመኖራቸው ጉዳዩ የፖለቲካ ቁርጠኝነትን የሚፈልግና በኮምሽኑ አቅም ብቻ መፍታት የማይቻል መሆኑንም ግለሰቡ ጠቅሰዋል፡፡
አቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ ጠ/ሚኒስትር ሆነው በተሾሙ ማግስት የገቢዎች ባለስልጣናትን በሙስና ከሰው ቢያሳስሩም ከዚያ በሁዋላ የተከሰሰ ሌላ ከፍተኛ ባለስልጣን የለም። አቶ ሃይለማርያም በገቢዎች ባለስልጣናት ላይ የተመሰረተው ክስ
በአቶ መለስ ዜናዊ ጊዜ የተጀመረ ነው በማለት ለእርሳቸው ተሰጥቶ የነበረው ምስጋና ወደ አቶ መለስ እንዲዞርላቸው ጠይቀው ነበር።
ጸረ ሙስና ኮሚሽን በቅርቡ በአገሪቱ ውስጥ ከፍተኛ ሙስና ይፈጸምበታል የሚባለውን በጄኔራል ክንፈ ዳኘው የሚመራው የብረታብረት ኢንጂነሪግ ኮርፖሬሽንን ጨምሮ በ በታላላቅ ኩባንያዎች ላይ ምርመራ መጀመሩን ቢያስታውቅም
የምርመራው ውጤት መቼ ይፋ እንደሚሆን አልገለጸም።


No comments:

Post a Comment