Wednesday, June 3, 2015

ወ/ሮ ንግስት ወንዲፍራው ክስ ተመሰረተባት

በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር

ሚያዝያ 14/2007 ዓ.ም በመንግስት ተጠርቶ ከነበረው ሰልፍ ጋር በተያያዘ በምርጫ ማግስት ግንቦት 19/2007 ዓ.ም ለእስር የተዳረገችው የሰማያዊ ፓርቲ አባል ወ/ሮ ንግስት ወንዲፍራው ክስ ተመሰረተባት፡፡
ዛሬ ግንቦት 26/2007 ዓ.ም በፌደራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ቂርቆስ ምድብ ችሎት የቀረበችው ወ/ሮ ንግስት፣ በፌደራል አቃቤ ህግ ከሳሽነት በ1996 ዓ.ም የወጣውን የወንጀል ህግ አንቀጽ 32/1/ሀ እና 490/3/ የተመለከተውን በመተላለፍ የሚል ክስ ቀርቦባታል፡፡
ወ/ሮ ንግስት ወንዲፍራው ሚያዝያ 14/2007 ዓ.ም በነበረው ሰልፍ ላይ ‹‹ወያኔ ሌባ፣ መንግስት አሸባሪ፣ ታርዷል ወገኔ፣ ይለያል ዘንድሮ የወያኔ ኑሮ፣ ወያኔ አሳረደን፣ ናና መንግስቱ ናና፣ ወያኔ አሸባሪ...በማለት እጅን አጣምሮ ወደላይ በማድረግ ታስረናል›› በማለት ሰላማዊ ሰልፉ እንዲታወክ አድርጋለች በሚል ተከሳለች፡፡ በተጨማሪም በሚያዝያ 13/2007 ዓ.ም ቂርቆስ አካባቢ ‹‹ስብሰባን ወይም ጉባኤን›› በማወክ እንደተከሰሰች የክስ ቻርጁ ያሳያል፡፡
ግንቦት 21 ቀን 2007 ዓ.ም ፍርድ ቤት በቀረበችበት ወቅት ፍርድ ቤቱ ለግንቦት 28/2007 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቶ የነበር ቢሆንም ‹‹በምስክሮች ላይ ማስፈራራት እየተፈጸመ ስለሆነና ምርመራየንም ስለጨረስኩ›› በሚል ፖሊስ ዛሬ ቤተሰቦቿ እንኳ ሳይሰሙ ወ/ሮ ንግስትን ፍርድ ቤት አቅርቦ ክስ መስርቶባታል፡፡
ወ/ሮ ንግስት ወንዲፍራው በቀጣይ አርብ ግንቦት 28/2007 ዓ.ም ለሶስተኛ ጊዜ ፍርድ ቤት ትቀርባለች ተብሎ ይጠበቃል፡፡



No comments:

Post a Comment