Monday, June 1, 2015

የመንግስት ወታደሮች በሞያሌና በኦጋዴን ሃይላቸውን እያጠናከሩ ነው

ግንቦት ፳፬ (ሃያ አራት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ባለፉት ሁለት ሳምንታት የኢትዮጵያ እና የኬንያ ድንበር የተለያዩ ግጭቶችን አስተናግዷል እንደ አይን ምስክሮች ገለጻ። ዩኒፎርም የለበሱ የኢትዮጵያ ወታደሮች ወደ ኬንያ በመግባት የኦሮሞ ነጻ አውጭ ግንባር አባላትን ለማደን ቢሞክሩም እስካሁን አልተሳካላቸውም። የመንግስት ወታደሮች ወደ ኬንያ ሞያሌ ከተማ በመግባት ቦሩ ሁካ የተባለ የ55 ዓመት የትምህርት ቤት ዘበኛ በጥይት በሳስተው ገድለውታል። ነዋሪዎች የኦነግ አባላት የሆኑ ታጣቂዎች የተደበቁበትን ቦታ እንዲያሳዩ ይገደዱ ነበር። ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ ኦነግ ወታደሮች ወደ ሞያሌ ከተማ በተከታታይ በመግባት ጥቃ
ት ካደረሱ በሁዋላ ወደ ኬንያ በመግባት ይሸሸጋሉ። በየጊዜው የሚደርሰውን ጥቃት ማስቆም ያልቻለው ኢህአዴግ መንግስት፣ የታጣቂዎች መደበቂያ ዋሻ ሆኗል ባለው የኬንያ ህዝብ ላይ እርምጃ እየወሰደ ነው።
በኬንያ ድንበር አካባቢ የሚንቀሳቀሱ ታጣቂዎችን እንዲወጉ ተልእኮ ተሰጥቷቸው ሲንቀሳቀሱ ከነበሩት መካከል 11 ወታደሮች እስከነመሳሪያቸው ሲጠፉ ፣ መረጃው የደረሳቸው አዛዦች ወታደሮች እንዲታደኑ አስደርገው 8ቱ ሲያዙ፣ ሁለቱ አምልጠዋል። አንዱ ደግሞ ቆስሎ ተይዟል። ወታደሮቹ የተቃዋሚ ሃይሎችን ለመቀላል እቅድ እንደነበራቸው መረጃዎች አመልክተዋል። ሁለቱ ያልተያዙት ወታደሮች የት እንደገቡ እስካሁን የታወቀ ነገር የለም።በኦጋዴን አካባቢ በኦብነግና በክልሉ ልዩ ሚሊሺያ መካከል በተካሄደው ጦርነት ደግሞ 6 የልዩ ሃይሉ ሚሊሺያ አባላት መያዛቸውን አንድ የሶማሊ ጋዜጣ ዘግቧል። ተያዙ ስለተባሉት የልዩ ሚሊሺያ አባላት ከመንግስት ወገን የተሰጠ
ማረጋገጫ የለም።የኦጋዴን ነጻ አውጭ ድርጅት ለኢሳት በላከው መግለጫ በኢትዮጵያ መንግስት ድጋፍ የሚሰለጥኑት ልዩ ፖሊስ የሚባሉት ሃይሎች ሺላቦ ወረዳ ላይ የዘር ማጥፋት ወንጀል መፈጸማቸውን ገልጿል።በመቶዎች የሚቆጠሩ ሲቪሎች መገደላቸውንና በርካታ ቤቶችም መቃጠላቸውን ግንባሩ በመግለጫው ጠቅሷል። 50 የሚሆኑ ሴቶች፣ ህጻናትና አዛውንቶች አካላቸው ተከታትፎ መገደላቸውንም ድርጅቱ ጠቅሷል። ከአምስት ቀናት በፊት የተጀመረው ጥቃት አሁንም ድረስ መቀጠሉን የሚገልጸው ኦብነግ፣ ላባባር፣ ዛዳህ ዛዳህ፣ ዞንዶሆውሪድ በሚባሉት የገጠር መንደሮች የተፈጸመው ጥቃት አስከፊ ነው ይላል።
የልዩ ሚሊሺያ አባላት ወደ አካባቢው በመሄድ የገንዘብ መዋጮ ለመሰብሰብ መሞከራቸውንና ከህዝቡ በኩል ያገኙት ምላሽ አሉታዊ በመሆኑ ተበሳጭተው በርካታ የአካባቢው ሽማግሌዎች አንገታቸው እንዲቀላ ውሳኔ ቢያስተላልፉም ህዝቡ እንደተቃወመና በዚህም የተነሳ ፖሊሶች እርምጃ መውሰድ እንደጀመሩ መግለጫው ያትታል። ከህዝብ በደረሰባቸው ጥቃት የተበሳጩት ፖሊሶች ራሳቸውን መከላከል ወደ ማይችሉት ሴቶችና ህጻናት ጠመንጃቸውን አዙረው ፊታቸው ላይ የቆመውን ሁሉ ገድለዋል ብሎአል መግለጫው።የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ለልዩ ፖሊሱ የምግብና የመሳሪያ እርዳታ በማድረግ በሚሸሹ ዜጎች ላይ ተጨማሪ እርምጃ እንዲወስድ እያበረታታው መሆኑን መግለጫው አክሎ ጠቅሷል።ኦብነግ ድርጊቱን በጥብቅ አውግዞ አለማቀፉ ማህበረሰብ አጣሪ ቡድን እንዲልክ ጠይቋል።በሌላ በኩል ደግሞ የኢትዮጵያ መንግስት ወታደሮች የቆሰሉ ነዋሪዎች ጉሪል በሚባል ከተማ ለመታከም ሲሄዱ፣ የኢትዮጵያ መንግስት ወታደሮች እንደከለከሉዋቸው ጎብጆብ ሬዲዮ ከሞቃዲሹ ዘግቧል። የኢስታርሊን ሆስፒታል ዳይሬክተር ኦማር ታራቢ 8 ሰዎች ወደ ሆስፒታሉ በመምጣት እርዳታ ቢጠይቁም የኢትዮጵያ ወታደሮች እርዳታ እንዳያገኙ መከላከላቸውን ተናግረዋል።ታራቢ እንደገለጹት በርካታ ቁስለኛ ሲቪሎችን የጫኑ መኪኖች ወደ ጉርኤል ከተማ እንዳይገቡ ተከልክለዋል። ሬዲዮው በአካባቢው ያለው ግጭት ተባብሶ መቀጠሉን ዘግቧል። የኢህአዴግ መንግስት በጉዳዩ ላይ እስካሁን የሰጠው መግለጫ የለም። አለማቀፍ ሰብአዊ መብት ድርጅቶች የመከላከያ ሰራዊቱ በኦጋዴን አካባቢ ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰት መፈጸሙን በተደጋጋሚ አጋልጠዋል።


No comments:

Post a Comment