Saturday, August 30, 2014

ስልጠና ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ተማሪዎች ጠንከር ያሉ ጥያቄዎችን ማንሳት መቀጠላቸውን ሰልጣኞቹ ገለጹ፡፡

‹‹ለግራዚያኒ ዘብ የቆመው ኢህአዴግ እንዴት ኢትዮጵያዊ ይባላል?››
Minilik Salsawi (ምንሊክ ሳልሳዊ) Via ነገረ ኢትዮጵያ / Negere Ethiopia

• ‹‹ተቃዋሚዎችን እያሰራችሁ እንዴት ተቃዋሚ የለም ትላላችሁ››
• ተማሪዎቹን በፖሊስና ደህንነት እያሸማቀቁ ነው
• ‹‹ብሄራዊ ቋንቋ የሌላት አገር ሉዓላዊ ልትባል አትችልም››
• ‹‹አንቀጽ 39 ከህገ መንግስቱ ይውጣ››
• ‹‹ለግራዚያኒ ዘብ የቆመው ኢህአዴግ እንዴት ኢትዮጵያዊ ይባላል?
• ተማሪዎቹን በፖሊስና ደህንነት እያሸማቀቁ ነው


ኢህአዴግን ደግፈው የሚከራከሩ ተማሪዎች ቁጥር በማነሱ ፖሊስና ደህንነቶች ሲቪል መስለው እንደሚከራከሩና የሚጠይቁትንና ጠንካራ አስተያየት የሚሰጡትን ተማሪዎች ለብቻቸው እየጠሩ እያሸማቀቁ መሆኑ ታውቋል፡፡ ሰልጣኝ ተማሪዎች የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ስልጠና ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ተማሪዎች ጠንከር ያሉ ጥያቄዎችን ማንሳት መቀጠላቸውን ሰልጣኞቹ ለነገረ ኢትዮጵያ ገለጹ፡፡ ባለፉት የስልጠና ጊዜያት ኢህአዴግን ላለፉት 23 አመታት አይተነው ለውጥ ስላላመጣ ስልጣን ሊለቅ ይገባል፣ የአሰብ ወደብ ለኤርትራ መሰጠቱ ስህተት ነው፣ የሸክ ኑሩ ግድያ ሴራ ነው፣ የባህርዳሩ ግጭት የብአዴን ሴራ ነው የመሳሰሉት ጥያቄዎች መነሳታቸው ይታወቃል፡፡ በአሁኑ ወቅትም ጠንከር ያሉ ጥያቄዎች እየተነሱ መሆናቸውን ሰልጣኞቹ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ የህገ መንግስት ማሻሻያ በደብረማርዎስ ከተማ የሚሰለጥኑ ተማሪዎች ህገ መንግስቱ ማሻሻያ እንዲደረግበት ጠይቀዋል፡፡

በተለይም አንቀጽ 39 ‹‹የኢትዮጵያ ህዝብ መካከል ልዩነት ለመፍጠር ህገ መንግስቱ ላይ የተቀመጠ አንቀጽ በመሆኑ ህገ መንግስቱን ለማሻሻል የተቀመጡት ውጣ ውረዶች ሳይገድቡት ከህገ መንግስቱ ሊወጣ ይገባል›› ብለዋል፡፡ በሌላ በኩል ‹‹አንቀጽ 39 እንዲሁ ከሚቀየር የኢትዮጵያ ህዝብ ህዝበ ውሳኔ አድርጎበት ከህገ መንግስቱ ቢወጣም የተሻለ ነው፡፡›› የሚል ሀሳብ ያቀረቡ እንደሚገኙበት ታውቋል፡፡ ብሄራዊ ቋንቋ ተማሪዎቹ ‹‹ኢትዮጵያን ያህል አገር ለምን ብሄራዊ ቋንቋ አይኖራትም?›› ብለው የጠየቁ ሲሆን አሰልጣኞቹ ኢትዮጵያ ብሄራዊ ቋንቋ የሌላት መሆኑን ተናግረው ከማለፍ ውጭ ለጥያቄው መልስ መስጠት እንደተቸገሩ ሰልጣኞቹ ገልጸዋል፡፡

ተማሪዎቹ በበኩላቸው ‹‹ህገ መንግስቱ ሲረቀቅ የብሄራዊ ቋንቋ ጉዳይ የተረሳው ሆን ተብሎ ነው፡፡ ብሄራዊ ቋንቋ የሌላት አገር ከሌሎች ብሄራዊ ቋንቋ ካላቸው አገራት ጋር እኩል ሉዓላዊ ልትሆን አትችልም›› ሲሉ አስተያየት መስጠታቸውን ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ ኢህአዴግ ኢትዮጵያዊ ነው? መጋቢት 6/2005 ዓ.ም ሰማያዊ ፓርቲ፣ ባለራይ ወጣቶችና በአቶ ታዴዎስ ታንቱ የተመራ የአገር ተቆርቋሪ አካል ለግራዚያኒ የቆመውን መታሰቢያ ተቃውሞ ስድስት ኪሎ በሚገኘው የሰማዕታቱ ሀውልት ጀምሮ ወደ ጣሊያን ኤምባሲ የሚያመራ ሰልፍ ጠርቶ ነበር፡፡ ይሁንና ሰልፉ ከመጀመሩ በፊት ፖሊስ ሰልፉን በኃይል በመበተን ተሳታፊዎቹን ማሰሩ ይታወቃል፡፡

በስልጠና ላይ የሚገኙት ተማሪዎቹም ‹‹ኢትዮጵያውያንን የቀጠፈውን የቅኝ ገዥ ጀኔራል ላይ ተቃውሞ እንዳይነሳ የፈለገና፣ በእሱ ላይ ተቃውሞ ሰልፍ ለመውጣት የሞከሩትን የደበደበና ያሰረው ኢህአዴግ እንዴት ኢትዮጵያዊ ሊባል ይችላል? ኢህአዴግ ለግራዚያኒ ጠበቃ ቆሞ እንዴት ኢትዮጵያዊ ይባላል?›› ይባላል የሚል ጥያቄ አንስተዋል፡፡ ተቃዋሚዎቹን እያሰራችሁ አሰልጣኞች ተቃዋሚ ፓርቲዎች በሰላማዊ ሰልፍም ሆነ በሌሎች አጋጣሚዎች የሚያነሷቸውን ጥያቄዎች ትክክል አለመሆናቸውን የገለጹ ሲሆን ጠንካራ ተቃዋሚ ፓርቲ እንደሌለም ተገልጾአል፡፡ በተቃራኒው ተማሪዎቹ በተቃዋሚዎቹ ላይ የሚደርስባቸውን ጫና እና የታሰሩትንም በምሳሌነት በማንሳት ‹‹ተቃዋሚዎቹን እያሰራች እንዴት ተቃዋሚ የለም ትላላችሁ? የሚል ጥያቄ አንስተዋል፡፡

ኢህአዴግ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዱን ለማሳካት አቅም እንደሌለውና አፋኝ እንደሆነ የሚገልጹ አስተያየቶችንም ተነስተዋል፡፡ ተማሪዎቹን ማሸማቀቁ ቀጥሏል በተለያዩ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲዎች የሚገኙ ሰልጣኝ ተማሪዎችን ጥያቄ እንዳይጠይቁ ማሸማቀቁ እንደቀጠለ ነው ተባለ፡፡ በተለይ በልደታ ግቢ በመሰልጠን ላይ የሚገኙ ተማሪዎች ጥያቄ ሲጠይቁም ሆነ አስተያየት ሲሰጡ ስለማንነታቸው አላስፈላጊ ዝርዝር ጥያቄዎችን እየተጠየቁ እንደሆነ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም ኢህአዴግን ደግፈው የሚከራከሩ ተማሪዎች ቁጥር በማነሱ ፖሊስና ደህንነቶች ሲቪል መስለው እንደሚከራከሩና የሚጠይቁትንና ጠንካራ አስተያየት የሚሰጡትን ተማሪዎች ለብቻቸው እየጠሩ እያሸማቀቁ መሆኑ ታውቋል፡፡

ከአፈናው በተጨማሪ በተለያዩ የአዲስ አበባ ክፍሎች የሚሰለጥኑትን ተማሪዎችን በመደለያነት ሙዚቃ፣ ከፍተኛ ወጭ የወጣበት ምግብና የመዝናኛ ምሽቶች እየተደረጉላቸው መሆኑን ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ በሌላ በኩል በመላ አገሪቱ በስልጠና ላይ ለሚገኙት ተማሪዎች ስልጠና የሚሰጡት ከወራት በፊት በመቀሌ ስልጠና የተሰጣቸው የገዥው ፓርቲ ካድሬዎች እንደሆኑ ለማወቅ ተችሏል፡፡


No comments:

Post a Comment