Monday, March 9, 2015

በኢትዮጵያ መንግሥት የሳይበር ጥቃት መፈፀሙ ይፋ ተደረገ

የኢትዮጵያ መንግስት የመረጃ ጠለፋ መፈጸሙን እንደገፋበት ሂዩማን ራይትስ ዎች ተናገረ፡፡ የሰብአዊ መብት ተሟጋቹ ድርጅት ዛሬ ይፋ አንዳደረገው ከሆነ መንግስት ቀስ በቀስ ጋዜጠኞችን ጸጥ ያደርጋል እንዲሁም የዲጂታል ጥቃት ይፈጽማል ሲል ገልጿል፡፡

የኢትዮጵያ የመረጃ ስለላ ተቋም

ባለፈው አመት “ዘይ ኖው ኤቭሪቲንግ ዊ ዱ፤የኢንተርኔትና የቴሌኮም ስለላ በኢትዮጵያ” ሲል ቡድኑ ባወጣው ዘገባ የኢትዮጲያ መንግስት በዜጎቹ ላይ የቴሌኮምና የመረጃ መረብ እያንዳንዱን ሚስጥራቸውን ይበረብራል ማለቱ አይዘነጋም፡፡

ዘንድሮም በተመሳሳይ መንግስት ይህን ድርጊት መፈጸሙን አጠናክሮ እንደቀጠለ የሚናገረው ቡድኑ በውጪ የሚኖሩ ነጻ ጋዜጠኞች ላይ ሳይቀር የሳይበር ጥቃት ይፈጽማል በማለት አትቷል፡፡

መሰረቱን በካናዳ ቶሮንቶ ያደረገ አንድ ገለልተኛ አጥኚ ቡድን ሰሞኑን በአንድ የሚዲያ ተቋም ላይ መንግስት የሳይበር ጥቃት መፈጸሙን ማረጋገጡን የሚገልጸው ሂዩማን ራይትስ ዎች ለኢትዮጵያ መንግስት የመረጃ መረብ መጥለፊያና ጥቃት መፈጸሚያ ምርቶችን የሚሸጡ አለም አቀፍ ኩባኒያዎች ድርጊቱን እንዲያጣሩ፤ድርጊቱን ፈጻሚው መንግስትም በአስቸኳይ ከድርጊቱ እንዲታቀብ አሳስቧል፡፡

ይህን የሂዩማን ራይትስዎች መረጃ ተከትሎ በርካታ አለም አቀፍ ሚዲያዎች ባወጡት ዘገባ የኢትዮጵያን መንግስት አውግዘዋል፡፡

ባለፈው አመት የኢትዮጵያ መንግስት ከአንድ የጣሊያን የደህንነት ተቋም በውጪ የሚኖሩ ጋዜጠኞችን ለመሰለል የሶውትዌር ምርት እንደገዛ በአንድ ገለልተኛ ቡድን ምርመራ መረጋገጡን በመጥቀስ ዘገባውን የሚጀምረው ማዘርቦርድ የተባለው የወሬ ምንጭ ይሁን እንጂ ዘንድሮም በተመሳሳይ መንግስት የሳይበር ጥቃቱን ቀጥሎበታል ሲል ያትታል፡፡ በዚህም ሰለባ ከሆኑት መካከል የኢትዮጵያ ሳተላይት ሬዲዮና ቴሌቪዥን(ኢሳት) እንዲሁም በውጭ የሚኖሩና በስራ ላይ ያሉ የኢትዮጵያውያን ነፃው ፕሬስ ጋዜጠኞች እንደሚገኙበት መዘገቡ አይዘነጋም፡፡

ይህን በሚመለከት ተመሳሳይ ዘገባ ይዞ የወጣው ዋሽንግተን ፖስት በበኩሉ የኢትዮጵያ መንግስት በውጪ ያሉ ነጻ ጋዜጠኞችን በሽብር ይከሳል አልፎ ተርፎም የሚያሰራጯቸውን የሚዲያ አገልግሎቶች ጃም በማድረግና በሳይበር ጥቃቶች ለማፈን ይሞክራል ማለቱን ድሬ ቲዩብ ዘግቧል፡፡


No comments:

Post a Comment