Thursday, March 12, 2015

በረከት ስምኦን ራሳቸውን ከምርጫ ክርክር አገለሉ

መጋቢት ፫(ሦስት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በአለማቀፍ ታዛቢዎችና በኢትዮጵያውያን በቂ ትኩረት ያልተሰጠውን የግንቦት 16 ቀን 2007 ምርጫ ክርክር የሚሳተፉለትን መሪዎች ሲያፈላል የነበረው ኢህአዴግ፣ ለመጀመሪያው ዙር የክርክር መድረክ የሚሆኑትን ሰዎች ሲመርጥ፣ አቶ በረከት ራሳቸውን አግልለዋል።
ኢህአዴግ 23 አመራሮችን ለክርክር በእቅድ የያዘ ቢሆንም፣ ከእነዚህ ወስጥ በመጀመሪያው ዙር መጣሪያውን ያለፉት አቶ ሬዲዋን ሁሴን እና አቶ ደሰታ አስፋው ብቻ ናቸው። 21ዱ አመራሮች ቀጥተኛ ተፎካካሪ መሆን አይችሉም ተብለዋል።
በሁለተኛው ዙር ማጣራት አቶ አባይ ፅሃየ ፣ካሳ ተክለብርሃን ፤ ተፈራ ደርበው ፤ሽመልስ ከማል እንዲያልፉ ተደርጓል። ኢህአዴግ የተቃዋሚ ፓርቲዎችን ማህደር ሲያጠና ከርሞ ዛሬ በዝግ ለተከራካሪ አመራሮች ገለጻ እያደረገ ነው።
በመጀመሪያው ዙር በእጩነት ቀርበው አይመጥኑም፣ ኢህአዴግን ያዋርዱታል ከተባሉት ውስጥ አባ ዱላ ገመዳ፣ አስቴር ማሞ፣ ዘነቡ ታደሰ፣ ሙፈሪያት ከማል፣ ከበደ ጫኔ፣ ወልዱ ይምሰል፣አህመድ አብተው፣ ተመስገን ጥላሁን፣ አሊ ሲራጅ፣ ታደሰ ሃይሌ፣ ፍሬህይወት አያሌውና ብስራት ጋሻው ይገኙበታል።

በረከት ስምኦን በክርክር መድረኮች ላይ እንዲገኙ ቢጠየቁም አልፈልግም በሚል ራሳቸውን አግልለዋል። ራሳቸውን ለማግለላቸው የሰጡት ምክንያት የለም። ከመጋቢት 04 ቀን 2007 ዓ.ም ጀምሮ በሚካሄደው የፓርቲዎች ክርክር ገዢው ፓርቲ ኢህአዴግን ጨምሮ በአንድ የክርክር መድረክ ላይ አምስት ፓርቲዎች የሚሳተፉ ሲሆን በአጠቃላይ ዘጠኝ መድረኮች ይካሄዳሉ።
ፓርቲዎቹ በተመረጡት አጀንዳዎች ላይ ያላቸውን አቋም በሚገባ ለማንጸባረቅ በአንድ የክርክር መድረክ የሚሳተፉት ፓርቲዎች ብዛት አምስት እንዲሆን ተደርጓል። በክርክሩ ላይ ተቃዋሚዎች እያንዳንዳቸው አንድ ተከራካሪ እና አንድ አማካሪ እንዲሁም ገዢው ኢህአዴግ ሁለት ተከራካሪና አንድ አማካሪ በመያዝ ይከራከራሉ። የዘንድሮውን ምርጫ የአውሮፓ ህብረት አይታዘበውም። ህብረቱ በምርጫው መሳተፍ ዋጋ የለውም በሚል ምክንያት መሆኑን በቅርቡ በህብረቱ ውስጥ በተዘጋጀ አንድ ዝግጅት ላይ ተገልጿል።


No comments:

Post a Comment